አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በመታጠቅ የበሽታ አምጪ ተህዋሲያን የዘረመል ጥናትና ትንተና አቅሙን እያሳደገ መሆኑን ገለጸ፡፡
ማዕከሉ የበሽታ አምጪ ተህዋሲያን የሆኑትን ቫይረስ እና ባክቴሪያ የዘረመል ትንተና በማካሄድ ቀድሞ መከላከል ብሎም ከተከሰቱ በኋላም አፋጣኝ መፍትሄዎችን መስጠት የሚያስችል መሆኑም ተጠቁሟል፡፡
ማዕከሉ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ ለፖሊሲ እና ለፕሮግራም ግብዓት የሚሆኑ መረጃዎችን ማቅረብ የሚያስችል ሲሆን በዘረመል ጥናትና ትንተና በአፍሪካ የልህቀት ማዕከል የመሆን ራዕይ አንግቦ እየሰራ ይገኛል፡፡
ተቋሙ ከዚህ ቀደም ለዘረመል ጥናትና ትንተና ወደ ወጭ ሀገራት ይላኩ የነበሩ ናሙናዎች በሀገር ውስጥ በማከናወን ለሚከሰቱ ወረርሽኞች አፋጣኝ ምላሽ በመስጠት ላይ እንደሚገኝም ተገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ጌታቸው ቶሌራ፤ ማዕከሉ ቴክኖሎጂን መጠቀሙ በሽታ አምጪዎችን ቀደሞ በመለየት እውቀትን መሠረት ያደረገ ምላሽ የመስጠት አቅሙ ማደጉን ገልጸዋል።
የሚገኙ የዘረመል ውጤቶች በሽታዎችን ቀድሞ ለመከላከል፣ ለይቶ ለማከም እንዲሁም ወረርሽኞች ሲከሰቱ ፈጥኖ መዘጋጀት የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡
በተለያየ መልኩ በሽታዎች በሚከሰቱበት ወቅት ዘመናዊ መሳሪያዎችን በመጠቀም ክትባቶችን ብሎም መድኃኒቶችን ለማዘጋጀት እንደሚረዳም ተናግረዋል፡፡
ተቋሙ ለዚህ የሚሆኑ ብቁ የሰው ኃይልን ጨምሮ አስፈላጊውን ግብዓት ማሟላት መቻሉን ተናግረዋል፡፡
ኢንስቲትዩቱ ከ32 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸውን ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች በመጠቀም በኦሮሚያ፣ አማራ፣ ትግራይ እና ሲዳማ ክልሎች ተጨማሪ ማዕከላትን ማደራጀቱን ተናግረዋል፡፡
ማዕከላቱ በቅርቡ ወደ ስራ እንደሚገቡ ጠቁመው፤ ተጨማሪ 30 የሚሆኑ ናኖፖል የተባሉ ዘረመል ጥናትና ትንተናን የሚያከናውኑ መሳሪያዎችን በማሰራጨት ላይ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡
የአርቦ ቫይረስና ሌሎች ቫይረሶች የበሽታዎች ምርምር ዲቪዢን ኃላፊ ዶክተር አብርሃም አሊ፤ ማዕከሉ የተሠጠውን ተልዕኮ ለማሳካት የዘረመል ጥናትና ትንተና ስራውን በሚገባ እያከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡
በዚህም በኤች አይ ቪ፣ በቲቢ፣ በኮሌራ፣ በኩፍኝ እንዲሁም በሌሎች የበሽታ አምጪ ተህዋሲያን ላይ የዘረመል ጥናትና ትንተና ስራዎች ለፖሊሲ ማውጣት እና ለፕሮግራም ግብዓት እንዲሆኑ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የበሽታ አምጪ ተህዋሲያን ጥናትና ትንተና ማዕከል አስተባባሪ አጽብሃ ገብረእግዚአብሔር፤ ሁሉም ዓይነት የቫይረስ እና ባክቴሪያ ተህዋሲያን ላይ የጥናትና ትንታና ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ አንስተዋል፡፡
ማዕከሉ ከሁሉም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚመጡ የዘርፉ ባለሙያዎች የጥናትና ምርምር ማዕከል በመሆን እያገለገለ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል፡፡
በበሽታ አምጪ ተህዋሲያን ጥናትና ትንተና ማዕከል የትንተና ባለሙያ ራጂ አቡበከር በበኩላቸው በአጭር ጊዜ ውስጥ በበርካታ ቫይረስ እና ባክቴሪያዎች ተህዋሲያን ላይ አመርቂ የሆነ የጥናትና ትንተና ስራዎች መስራታቸውን ተናግረዋል፡፡
ማዕከሉ በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና እንዲያገኝ ከአፍሪካ የሜዲካል ላቦራቶሪ ጋር በመሆን እየተሰራ እንደሚገኝ ተጠቁሟል።
ቦንጋ ፤የካቲት 16/2017 (ኢዜአ) ፡-በቦንጋ ከተማ የተካሄደውን የህዝብ ውይይት የመሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች በከተማው የተለያዩ የልማት ...
Feb 24, 2025
ደብረብርሀን፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ገበያን ለማረጋጋት የሚያግዙ ከአንድ ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የገበያ ማዕከላት ግንባታ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- በሚቀጥሉት አምስት አመታት በወረቀት የሚካሔዱ አሰራሮችን በማስቀረት የዲጂታል ቴክኖሎጂ ግብይትና አገልግሎት በተሻለ ...
Feb 8, 2025