የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የበሽታ አምጪ ተህዋሲያን ጥናትና ትንተና አቅሙን እያሳደገ ነው

May 15, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በመታጠቅ የበሽታ አምጪ ተህዋሲያን የዘረመል ጥናትና ትንተና አቅሙን እያሳደገ መሆኑን ገለጸ፡፡

ማዕከሉ የበሽታ አምጪ ተህዋሲያን የሆኑትን ቫይረስ እና ባክቴሪያ የዘረመል ትንተና በማካሄድ ቀድሞ መከላከል ብሎም ከተከሰቱ በኋላም አፋጣኝ መፍትሄዎችን መስጠት የሚያስችል መሆኑም ተጠቁሟል፡፡

ማዕከሉ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ ለፖሊሲ እና ለፕሮግራም ግብዓት የሚሆኑ መረጃዎችን ማቅረብ የሚያስችል ሲሆን በዘረመል ጥናትና ትንተና በአፍሪካ የልህቀት ማዕከል የመሆን ራዕይ አንግቦ እየሰራ ይገኛል፡፡

ተቋሙ ከዚህ ቀደም ለዘረመል ጥናትና ትንተና ወደ ወጭ ሀገራት ይላኩ የነበሩ ናሙናዎች በሀገር ውስጥ በማከናወን ለሚከሰቱ ወረርሽኞች አፋጣኝ ምላሽ በመስጠት ላይ እንደሚገኝም ተገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ጌታቸው ቶሌራ፤ ማዕከሉ ቴክኖሎጂን መጠቀሙ በሽታ አምጪዎችን ቀደሞ በመለየት እውቀትን መሠረት ያደረገ ምላሽ የመስጠት አቅሙ ማደጉን ገልጸዋል።

የሚገኙ የዘረመል ውጤቶች በሽታዎችን ቀድሞ ለመከላከል፣ ለይቶ ለማከም እንዲሁም ወረርሽኞች ሲከሰቱ ፈጥኖ መዘጋጀት የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡

በተለያየ መልኩ በሽታዎች በሚከሰቱበት ወቅት ዘመናዊ መሳሪያዎችን በመጠቀም ክትባቶችን ብሎም መድኃኒቶችን ለማዘጋጀት እንደሚረዳም ተናግረዋል፡፡

ተቋሙ ለዚህ የሚሆኑ ብቁ የሰው ኃይልን ጨምሮ አስፈላጊውን ግብዓት ማሟላት መቻሉን ተናግረዋል፡፡

ኢንስቲትዩቱ ከ32 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸውን ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች በመጠቀም በኦሮሚያ፣ አማራ፣ ትግራይ እና ሲዳማ ክልሎች ተጨማሪ ማዕከላትን ማደራጀቱን ተናግረዋል፡፡

ማዕከላቱ በቅርቡ ወደ ስራ እንደሚገቡ ጠቁመው፤ ተጨማሪ 30 የሚሆኑ ናኖፖል የተባሉ ዘረመል ጥናትና ትንተናን የሚያከናውኑ መሳሪያዎችን በማሰራጨት ላይ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡

የአርቦ ቫይረስና ሌሎች ቫይረሶች የበሽታዎች ምርምር ዲቪዢን ኃላፊ ዶክተር አብርሃም አሊ፤ ማዕከሉ የተሠጠውን ተልዕኮ ለማሳካት የዘረመል ጥናትና ትንተና ስራውን በሚገባ እያከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡

በዚህም በኤች አይ ቪ፣ በቲቢ፣ በኮሌራ፣ በኩፍኝ እንዲሁም በሌሎች የበሽታ አምጪ ተህዋሲያን ላይ የዘረመል ጥናትና ትንተና ስራዎች ለፖሊሲ ማውጣት እና ለፕሮግራም ግብዓት እንዲሆኑ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የበሽታ አምጪ ተህዋሲያን ጥናትና ትንተና ማዕከል አስተባባሪ አጽብሃ ገብረእግዚአብሔር፤ ሁሉም ዓይነት የቫይረስ እና ባክቴሪያ ተህዋሲያን ላይ የጥናትና ትንታና ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ አንስተዋል፡፡

ማዕከሉ ከሁሉም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚመጡ የዘርፉ ባለሙያዎች የጥናትና ምርምር ማዕከል በመሆን እያገለገለ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል፡፡

በበሽታ አምጪ ተህዋሲያን ጥናትና ትንተና ማዕከል የትንተና ባለሙያ ራጂ አቡበከር በበኩላቸው በአጭር ጊዜ ውስጥ በበርካታ ቫይረስ እና ባክቴሪያዎች ተህዋሲያን ላይ አመርቂ የሆነ የጥናትና ትንተና ስራዎች መስራታቸውን ተናግረዋል፡፡

ማዕከሉ በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና እንዲያገኝ ከአፍሪካ የሜዲካል ላቦራቶሪ ጋር በመሆን እየተሰራ እንደሚገኝ ተጠቁሟል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.