
አዳማ ፤ሐምሌ 17/2017(ኢዜአ)፦በአዳማ ከተማ አስተዳደር የሌማት ትሩፋት ትግበራ የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ለስራ እድል ፈጠራ ተጨማሪ አቅም መፍጠሩን የከተማዋ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለፀ።
የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ አለሙ ቂልጡ ለኢዜአ እንደገለጹት በአዳማ ከተማ ባለፉት ሶስት ዓመታት በዘመናዊ እንስሳት እርባታ፣ በእንስሳት ማድለብ፣ በሰብልና በፍራፍሬ ልማት ስራዎች በርካታ ውጤቶች ተገኝተዋል።
በዚህም ጥቅም ላይ ያልዋሉ ሀብቶች ለሥራ እድል ፈጠራና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ተጨማሪ አቅም መፍጠራቸውን ተናግረዋል።

ለአብነትም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ በከተማ ግብርና ለ35 ሺህ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ገልፀዋል።
የስራ እድል ፈጠራውን ለማሳካትም በመንግስትና በማህበረሰቡ ተሳትፎ 2 ሺህ 500 ሼዶች መገንባታቸውንና የተሻሻሉ ዝርያ ያላቸው የወተት ላሞችና ዶሮዎች መሰራጨታቸውን ጠቅሰዋል።

በዓሣ ሀብት ልማቱ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ በተሰራው ስራ 154 የዓሳ ማራቢያ ኩሬዎችን በመገንባት ለወጣቶች ማስተላለፍ መቻሉን ተናግረዋል።

ዘመናዊ የንብ እርባታን ለማስፋፋትም ከተለያዩ አካላት ጋር በመቀናጀት 11 ሺህ ዘመናዊ የንብ ቀፎዎች እንዲሰራጩ መደረጉን አመልክተዋል።
የፍራፍሬ ልማትን ለማሳካት ከምርምር ተቋማት ጋር በመተባበር የተሻሻሉ ምርጥ ዘሮችን በማቅረብና የአዋሽ ወንዝን በመጥለፍ በማህበር የተደራጁ አርሶ አደሮችና ወጣቶች በፓፓዬ፣ በሙዝ፣ በብርቱካንና በአቮካዶ ልማት ላይ መሰማራታቸውን አስረድተዋል።

የከተማ አስተዳደሩ የስራ እድል ከፈጠረላቸው ወጣቶች መካከል በወንጂ ኩሪፍቱ ክፍለ ከተማ የ''ዴይሊ ፊሽ ማህበር'' አባል ወጣት በዛወርቅ አጥላው ከአምስት የዩኒቨርሲቲ ምሩቃን ጓደኞቹ ጋር በማህበር በመደራጀት በዓሣ እርባታ ስራ ላይ መሰማራታቸውን ገልጿል።
ለዚህም ከተማ አስተዳደሩ በሰጣቸው 40 የዓሣ ኩሬዎች ውስጥ ከዝዋይ ሀይቅ ያስመጧቸውን የዓሳ ጫጩቶች እያረቡ መሆናቸውን አስረድቷል።

በከተማዋ ''የማትናደፍ ንብና የማር ምርት ማህበር'' ሊቀመንበር ዮናስ ገብረኪሮስ በበኩላቸው ከከተማ አስተዳደሩ በተረከቡት ሼድ ዘመናዊ፣ ባህላዊና የሽግግር ቀፎ ንብ ማነብ መጀመራቸውን ገልጸዋል።
በዓመቱም በሁለት ዙር ጥራቱን የጠበቀ እስከ 2 ሺህ 500 ኪሎ ግራም የሚደርስ ማር በማምረት ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ስራቸውን ለማስፋፋት የከተማ አስተዳደሩ ባዘጋጀላቸው 5 ሺህ ካሬ ቦታ ላይ የሚያርፍ የፕሮጀክት ግንባታ ለማካሄድ ዝግጅት ማድረጋቸውን አስረድተዋል።
በፕሮጀክቱ በ1 ሼድ እስከ 200 የንብ ቀፎ ማስተናገድ የሚያስችል ባለ አራት ወለል ህንጻ በመገንባት ''የንግስት ንብ እርባታና የንብ ምርምር ማእከል'' ለመገንባት ማቀዳቸውን ተናግረዋል።
ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በኦዲት ዘርፍ በተከናወኑ የሪፎርም ተግባራት ተጨባጭ ለውጦች እየተመዘገቡ መሆናቸውን የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ...
Apr 22, 2026
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በምግብ ዋስትና እና በኢኮኖሚ ልማት ዘርፍ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራት ለመላው አፍሪካ አገራት ትልቅ አ...
Apr 16, 2026
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ለውጡ የሀገሪቱን ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ስብራቶች በመጠገን፣ ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ከፍታና ለማህበራዊ ትስስ...
Apr 3, 2026
ቦንጋ ፤የካቲት 16/2017 (ኢዜአ) ፡-በቦንጋ ከተማ የተካሄደውን የህዝብ ውይይት የመሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች በከተማው የተለያዩ የልማት ...
Feb 24, 2025