የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የገጠሩን ማህበረሰብ ኑሮ የመቀየር ስራ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና ባጠረ ጊዜ ማሳካት የሚያስችል ነው - አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ

Oct 31, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 20/2018 (ኢዜአ):- የገጠሩን ማህበረሰብ ኑሮ የመቀየር እና ምርታማነትን የማሳደግ ተግባር የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና ባጠረ ጊዜ ማሳካት የሚያስችል መሆኑን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ትናንት በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የክረምት ስንዴ ምርት አሰባሰብን ጎብኝተው የበጋ ስንዴ እርሻ ሥራን ማስጀመራቸው ይታወቃል።

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ከጉብኝቱ በኋላ በሰጡት አስተያየት የገጠሩን ማህበረሰብ ኑሮ የመቀየር ስራ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና ባጠረ ጊዜ ማሳካት የሚያስችል ነው ብለዋል።

መንግስት ከተሞችን የመቀየር እና ለነዋሪዎች ምቹ የማድረግ እንዲሁም የስራ ዕድል ፈጠራን ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል።


በተያዘው በጀት ዓመት በርካታ ቤቶችን ለመገንባት ታቅዶ ወደ ስራ መግባቱን አንስተው በኢትዮጵያ አብዛኛው ማህበረሰብ የሚኖረው በገጠር ክፍል መሆኑንና መንግስት በገጠር የሚኖሩ ዜጎችን ኑሮ ለመቀየር እና ምርታማነት ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

በገጠሪቱ የኢትዮጵያ ክፍል በአትክልት፣ ፍራፍሬና ሰብል እጅግ አበረታች ውጤት መገኘቱንና የምስራቅ ሸዋ ዞን የስንዴ ምርት ስራ የሚያመላክተው ይህንኑ ነው ብለዋል።

በዞኑ ያለው የኩታ ገጠም የስንዴ እርሻ በኮምባይነር እየታጨደ መሆኑን በማንሳት ይህም ትልቅ ተስፋ የሚሰጥ እንደሆነ ነው አፈ ጉባኤው የገለጹት።

ኢትዮጵያ ስንዴ፣ ሩዝ እና አቮካዶን ጨምሮ በተለያዩ ምርቶች ራሷን ለመቻል እያከናወናቸው ያለው ስራ አመርቂ ውጤት እየተመዘገበበት መሆኑን አመልክተዋል።

ኢትዮጵያ ስንዴ ከመግዛት ተላቃ በራሷ የማምረት አቅም ማሳደጓ የዚሁ ስራ ማሳያ ነው ብለዋል።

የተጀመረውን ስራ አጠናክሮ በመቀጠል በአጭር ጊዜ ውስጥ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ የሚደረገው ጉዞ ማሳካት እንደሚቻል ተናግረዋል።

በኦሮሚያ ክልል በገጠር ትራንስፎርሜሽን እየተከናወነ ያለው ስራ በሌሎች ክልሎችም እየተከናወነ መሆኑን በመጥቀስም ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ ያለው ስራ ውጤታማ መሆኑን አመልክተዋል።

የገጠሩን ክፍል ለመቀየር እየተከናወነ ያለው ስራ እጅግ ተስፋ የሚሰጥና አበረታች መሆኑንና ተደራሽነቱን በማስፋት የኢትዮጵያን ብልጽግና በአጠረ ጊዜ እንደሚሳካ አያጠራጥርም ነው ያሉት።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.