የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

አርሶ አደሮች በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በንብ ማነብ ስራ ላይ ተሰማርተው ውጤታማ ሆነዋል 

Dec 2, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

ቦንጋ፤ ሕዳር 23/2018 (ኢዜአ)፦በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በንብ ማነብ ስራ ተሰማርተው ውጤታማ መሆናቸውን በካፋ ዞን የጊምቦ ወረዳ አርሶ አደሮች ተናገሩ፡፡

የ ሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር ዋነኛ ዓላማ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ፤ በተለይም ስጋ፣ እንቁላል፣ ማር እና ወተት ቅንጦት ሳይሆን ትርፍ ምርት ሆነው እንዲገኙ ማድረግ ነው።

ሁሉም በየአካባቢው ያለውን ፀጋ ካለማ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች የቅንጦት ምግቦች ሳይሆኑ ከሌማት የማይጠፉ፣ በዕለታዊ ምግቦች ማባያነት የማይታጡ ግብዓቶች ማድረግ ይቻላል።

በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ከፋ ዞን የጊምቦ ወረዳ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ መርሃ ግብሩ ንብ የማነብ ስራቸውን ውጤታማነት በማረጋገጥ ከምርቱ ተገቢውን ጥቅም እንዲያገኙ እያስቻለ ነው፡፡


በመርሃ ግብሩ በንብ ማነብ ስራ ላይ ተሰማርተው ውጤታማ በመሆን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ገልጸዋል።

ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አርሶ አደር በላይ ባዬ፤ በጓሯቸው አስራ አምስት የሚጠጉ ዘመናዊና ባህላዊ ቀፎዎችን በመስቀል ከአንዱ ቀፎ ከ35 ኪሎ ግራም በላይ ማር እንደሚያገኙ ተናግረዋል፡፡


ከዚህ ቀደም ባህላዊ የንብ ማነብ መንገድ ይከተሉ እንደነበር ገልፀው በመርሃ ግብሩ በመታቀፍ ባገኙት ሙያዊ ድጋፍ ዘመናዊ የንብ ማነብ ስነ-ዘዴን በመከተላቸው የተሻለ ምርት እያገኙ መሆኑን አስረድተዋል።

አርሶ አደር ዘውዲቱ ገብሬ በበኩላቸው ፤አካባቢያቸው የማር መንደር ሆኖ ከተደራጀ ወዲህ በሚደረግላቸው ድጋፍ ታግዘው ማር በማምረት በሚያገኙት ገቢ ሕይወታቸውን በተሻለ መንገድ ለመምራት እንዳስቻላቸው ጠቁመዋል።


ከሀያ በላይ ባህላዊና ዘመናዊ ቀፎ እንዳላቸው ጠቅሰው፣ ከአንድ ዘመናዊ ቀፎ እስከ 35 ኪሎ ግራም ከባህላዊ ደግሞ ከ20 ኪሎ ግራም በላይ ምርት እያገኙ መሆናቸውንም ገልፀዋል።

መንግስት በሰጣቸው ቀፎ ታግዘው ወደ ንብ ማነብ ስራ መግባታቸውን የገለጸችው ደግሞ ወጣት አርሶ አደር ታየች ገብሬ ናት።

የማር ምርት በመሸጥ፣ በወተትና በዶሮ እርባታ ስራ ላይ የመሰማራት ዕቅድ እንዳላትም ወጣቷ አርሶ አደር ተናግራለች።


የካፋ ዞን ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ መምሪያ የእንስሳትና ዓሳ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አረጋ እንደገለፁት፤ በዞኑ የማር ምርታማነትን ለመጨመርና ጥራቱን ለማስጠበቅ 430 መንደሮችን በማደራጀት ዘርፈ ብዙ ድጋፎች እየተደረጉ ነው፡፡

በዚህም የማር ምርታማነት እድገት እያሳየ ሲሆን ባለፈው ዓመት 24 ሺህ 298 ቶን ማር መመረቱን ገልጸው ዘንድሮ የምርት መጠኑ ከ28 ሺህ ቶን በላይ ማደጉንና ጥራቱን የጠበቀ ማር ለማምረት ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።


ለተያዘው እቅድ ስኬት ግብዓት የማሟላት ስራ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው በተያዘው ዓመትም 33 ሺህ ዘመናዊ፣ ባህላዊ፣ የጨፈቃና የሽግግር ቀፎዎች ይሰራጫሉ ብለዋል፡፡

በእስካሁኑ ሂደትም ከ13 ሺህ 800 በላይ ቀፎዎች የተሰራጩ ሲሆን በ16 ሺህ ቀፎዎች ላይ ንብ የማዛወር ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.