የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

በዞኑ በአራት የወረዳ ከተሞች ህብረተሰቡን ያሳተፈ የኮሪደር ልማት ስራ እየተካሄደ ነው

Dec 11, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

ጎንደር ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በአራት የወረዳ ዋና ከተሞች ህብረተሰቡን ያሳተፈ የኮሪደር ልማት ስራ መጀመሩን የዞኑ ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ አስታወቀ፡፡

በክልሉ የከተሞችን ገፅታ ለመቀየርና ልማታቸውን ለማፋጠን በባህር ዳር፣ በጎንደር፣ በደሴ፣ በደብረ ብርሃን፣ በኮምቦልቻ፣ በደብረ ማርቆስና በሌሎች ከተሞች የኮሪደር ልማቱ በፍጥነት እየተከናወነ ይገኛል።

በዞኖቹ ኮሪደር ልማት የተገኘውን ተሞክሮ በማስፋትም በወረዳ ከተሞችና በገጠር ኮሪደር ልማት በማስፋት እየተከናወነ መሆኑም ተመላክቷል።

የዚሁ ተግባር አካል የሆነው የኮሪደር ልማት በአይከል፣ በሻውራ፣ በቆላድባና በአምባ ጊዮርጊስ ከተሞች እየተከናወነ እንደሚገኝ የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ዳንኤል ወርቁ ተናግረዋል፡፡

በከተሞቹ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት ስራ ህብረተሰቡ 70 በመቶ የሚሆነውን ወጪ በራሱ ለመሸፈን ቃል በገባው መሰረት ወደ ስራ ተገብቷል ነው ያሉት።

የከተሞቹን የወደፊት እድገት ታሳቢ በማድረግ በተዘጋጀ ዲዛይን መሰረት ወደ ስራ መገባቱን ጠቁመው አመራሩና ባለሙያው ከጎንደር ከተማ የኮሪደር ልማት ስራ ልምድ እንዲቀስም ተደርጓል ብለዋል፡፡

የኮሪደር ልማቱ የከተሞቹ ለኑሮ፣ ለስራና ለትራፊክ እንቅስቃሴ እንዲሁም ለንግድ ስራ አመቺ ያልነበረውን ዲዛይን በመቀየር ትልቅ አቅም አለው ብለዋል።

በኮሪደር ልማቱ ጠባብ መንገዶችን የማስፋት፣ የእግረኛ መንገዶችንና አረንጓዴ ስፍራዎችን የመገንባት እንዲሁም የኮንቴይነር ሱቆችን በማንሳት ደረጃቸውን የጠበቁ የገበያ ቦታዎችን የማደራጀት ስራዎች እየተካሄዱ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

ልማቱ የህብረተሰቡን የቆየ ልማዳዊ አስተሳሰብ በአዲስ በመቀየር ለስራ ያነሳሳ ትልቅ ተግባር ነው ያሉት ደግሞ የቆላድባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ታምራት አስረሳኸኝ ናቸው፡፡

ከተማ አስተዳደሩ የኮሪደር ልማት ስራው ለከተማው ልማትና እድገት መፋጠን የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ በመገንዘብ ህብረተሰቡን በማወያየት ወደ ስራ መግባቱን ተናግረዋል፡፡

ከተማውን በሚመጥን ደረጃ የተዘጋጀውን ዲዛይን መሰረት በማድረግ ወደ ስራ መገባቱን ጠቁመዋል፡፡

የኮሪደር ልማቱ ለከተሞች አዲስ ገጽታን በማላበስ ንጹህና አረንጓዴ ስፍራ አስፈላጊ መሆኑን በማህበረሰቡ ዘንድ ግንዛቤ የፈጠረ ታላቅ ተግባር ነው ያሉት የቆላድባ ከተማ ነዋሪ አቶ አስረስ አሸናፊ ናቸው፡፡

የከተማው ነባር ቤቶች የግንባታ አሰራር ለእሳት አደጋ ተጋላጭ የነበረ መሆኑን ጠቁመው፤ የኮሪደር ልማቱ የእሳት አደጋዎችን የሚቀንስና የሚያስቀር መሆኑን ተገንዝቤአለሁ ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.