የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

የዲጂታል ሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አንድ ሰው አንድ ማንነት እንዲኖረው ያስችላል

Jan 9, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦የዲጂታል ሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አንድ ሰው አንድ ማንነት እንዲኖረው በማድረግ ትክክለኛ ፖሊሲ መቅረጽ የሚያስችል መሆኑን የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ገለጸ፡፡

የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት በአዋጅ ቁጥር 1370/2017 መሰረት ከፌደራል እስከ ታችኛው የአስተዳደር እርከን ድረስ ራሱን የቻለ አደረጃጀት ያለው ሆኖ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ የማከናወን፣ የመምራት፣ የማስተባበር፣ የመደገፍ፣ የምዝገባ መረጃዎችን የማስተዳደር እና የማደራጀት፣ በብሔራዊ ደረጃ በመረጃ ቋት አደራጅቶ የመያዝ ሀላፊነት ተሰጥቶታል።

አገልግሎቱ በተሰጠው ስልጣን መሰረተ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ውክልና በመስጠት በመዲናዋ ሁሉም ወረዳዎች የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ማከናወን ጀምሯል፡፡

የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቢቂላ መዝገቡ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ የወረቀት አሰራርን በመቀየር አንድ ሰው አንድ ማንነት እንዲኖረው ያደርጋል፡፡

ከዚህ ቀደም በነበረው የማኑዋል/የወረቀት አሰራር አንድ ሰው ሁለት ቦታ የልደት፣ የሞትና መሰል የወሳኝ ሁነት የምስክር ወረቀት ያወጣ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

በዚህም በተጭበረበረ መረጃ የተሰሩ የወሳኝ ሁነት መረጃዎች መንግስት ለሚያሳልፋቸው የፖሊሲ ውሳኔዎች አስቸጋሪ ሆነው መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡

የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ የባዮሜትሪክና ባዮግራፊክ መረጃ እንደሚይዝ ገልጸው፤ የባዮሜትሪክ መረጃዎችን ከብሔራዊ መታወቂያ ጋር እንዲተሳሰር ይደረጋል ብለዋል፡፡

በዚህም አንድ ሰው አንድ ሆኖ የሚታወቅባትን ኢትዮጵያ መፍጠር የሚያስችል እንቅስቃሴ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የባዮሜትሪክና ባዮግራፊክ መረጃዎችን በማቀናጀት የአንድን ሰው ትክክለኛ ማንነት የሚገልጹ መሆናቸውን የገለጹት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፤ የአንድን ሰው ዜግነት መለየትም ያስችላሉ ብለዋል፡፡

እነዚህ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ መረጃዎችን በኩነት ምዝገባና እና በብሄራዊ መታወቂያ /ፋይዳ/ አማካኝነት መሰብሰብ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ማከናወን የሚያስችል መተግበሪያ በኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት አማካኝነት ለምቶ ወደ ሥራ መግባቱንም ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.