የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

ኢትዮጵያ እና ሳዑዲ አረቢያ በንግድና ገበያ ዕድል ድርድር ዙሪያ መከሩ

Mar 25, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና ሳዑዲ አረቢያ በንግድና ገበያ ዕድል ድርድር ዙሪያ ምክክር አድርገዋል።

14ኛው የዓለም ንግድ ድርጅት(WTO) የሚኒስትሮች ጉባኤ (MC14) በካሜሮን ያውንዴ እየተካሄደ ይገኛል።

የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ(ዶ/ር) ከጉባኤው ጎን ለጎን ከሳዑዲ አረቢያ የዓለም አቀፍ ስምምነቶችና ድርጅቶች ምክትል ገዥ እና የድርድር ቡድን መሪ ፋሪድ አል-አሳሊ ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አድርገዋል።


ውይይቱ በዋናነት ያተኮረው በሁለቱ ሀገራት መካከል ባለው የገበያ ዕድል ድርድርና የንግድ ልውውጥን ይበልጥ ማሳደግ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ነው።

ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ወደ ዓለም ንግድ ድርጅት ለመቀላቀል የምታደርገውን ድርድር በፈረንጆቹ 2026 ለማጠናቀቅ ያላትን ጽኑ አቋምና ዝግጁነት አብራርተዋል።

ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን የምታደርገው ጥረት ማጠናቀቂያው ላይ በደረሰበት በዚህ ወቅት፣ እንደ ሳዑዲ አረቢያ ካሉ ጠንካራ የንግድ አጋሮች ጋር የሚደረጉ የሁለትዮሽ ድርድሮች ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ እድገትና ለንግድ ስርዓቱ መዘመን ትልቅ ፋይዳ እንዳላቸው ተገልጿል።


በመጪው ሚያዚያ ወር በጄኔቫ ከሚካሄደው የሥራ ቡድን ስብሰባ በፊት የሁለትዮሽ የገበያ ዕድል ስምምነቱን ለማጠናቀቅ ቀጣይ የቴክኒክ ድርድሮች በፍጥነት እንዲከወኑ በሁለቱ ወገኖች መካከል መግባባት ላይ ተደርሷል።

ዲፕሎማሲያዊ ጥረቱ ኢትዮጵያ ወደ ዓለም አቀፍ የንግድ ሥርዓት ለመቀላቀል የምታደርገውን ጉዞ የሚያፋጥንና የሀገሪቱን የንግድ ጥቅሞች ይበልጥ የሚያረጋግጥ መሆኑን ኢዜአ ከንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ያገኘው መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.