🔇Unmute
ሆሳዕና፤ ሚያዚያ 5/2018 (ኢዜአ)፦ በሆሳዕና ከተማ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት የከተማዋን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ እያቀላጠፈ መሆኑን ነዋሪዎች ገለጹ።
በከተሞች ተግባራዊ የተደረገው የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ምቹ ከተሞችን ለመፍጠር የላቀ ድርሻ እያበረከተ ይገኛል።
በተለይም ቀደም ሲል በከተሞች ይስተዋል የነበረውን የመሠረተ ልማት ቅንጅት ማነስ በማስቀረት፣ በቴክኖሎጂ የተደገፈና የተቀናጀ ከተማ ለመገንባት መሠረት እየጣለ ነው።
በሆሳዕና ከተማ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማትም ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ የከተማዋ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ እንዲቀላጠፍ ማስቻሉን ነዋሪዎች ይናገራሉ።
አስተያየታቸውን ከሰጡ ነዋሪዎች መካከል የቦቢቾ ቀበሌ ነዋሪው አቶ ደስታ ኤርቻዮ፤ ልማቱ የነዋሪውን ዘርፈ ብዙ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ይገኛል ብለዋል።

የኮሪደር ልማቱ ለነዋሪው ምቹ የመኖሪያና የመዝናኛ ስፍራዎችን ማስገኘቱን ጠቅሰው፣ ልማቱ ከተማዋን ከመቀየር ባለፈ ቀደም ሲል በምሽት ለመንቀሳቀስ ሥጋት የነበሩ አካባቢዎችን ችግር መቅረፉንና ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ለማድረግ የሚያግዙ ማዘውተሪያዎችን በማካተቱ ዜጎች ጤናቸውን እንዲጠብቁ ማገዙን ገልጸዋል።
የአራዳ ቀበሌ ነዋሪው አቶ ጌታሁን አበራ በበኩላቸው፣ ልማቱ ከተማዋ ውበት እንድትላበስ ከማድረጉም ባለፈ የመንገድና የመብራት ችግሮች እንዲቀረፉ አድርጓል ብለዋል።

ልማቱ በእግር ለመጓዝ በሚያመች መልኩ በመቀየሩና የከተማዋን የጽዳት ሥርዓት በማሻሻሉ መንግሥት ለሕዝቡ የገባውን ቃል በተግባር ያረጋገጠበት ሥራ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ሌላኛዋ ነዋሪ ወይዘሮ ታገሰች ጋርከቦ ፤ ልማቱ በእግር ተንቀሳቅሰው ማኅበራዊ ጉዳዮቻቸውን እንዲያስፈጽሙ ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ገልጸዋል።

ወጣት ስንዳው ጀንበሩ ደግሞ የብስክሌት መንገድ መገንባቱ የትራፊክ መጨናነቅን ከመቀነሱም በላይ ብስክሌት አሽከርካሪዎች ያለምንም ሥጋት እንዲንቀሳቀሱ አስችሏል ብሏል።

የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሽጉጤ እንደገለጹት፤ የከተማውን የውስጥ አቅምና የማኅበረሰቡን ተሳትፎ በማቀናጀት የ35 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ለመሥራት ታቅዶ ወደ ትግበራ ተገብቷል።

በመጀመሪያው ምዕራፍ ከታቀደው 24.5 ኪሎ ሜትር ውስጥ 12 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትሩ ተጠናቆ ለአገልግሎት የበቃ ሲሆን፣ ሥራው ምቹ የእግረኛ መንገዶችን፣ የአካል ጉዳተኞች መሄጃን፣ የብስክሌት መንገድንና የመብራት መሠረተ ልማቶችን ያካተተ ነው ብለዋል።
ልማቱ የአካባቢን ጽዳት ባህል ከመቀየር ባለፈ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ከንቲባው አክለው ገልጸዋል።
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ለውጡ የሀገሪቱን ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ስብራቶች በመጠገን፣ ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ከፍታና ለማህበራዊ ትስስ...
Apr 3, 2026
ቦንጋ ፤የካቲት 16/2017 (ኢዜአ) ፡-በቦንጋ ከተማ የተካሄደውን የህዝብ ውይይት የመሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች በከተማው የተለያዩ የልማት ...
Feb 24, 2025
ደብረብርሀን፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ገበያን ለማረጋጋት የሚያግዙ ከአንድ ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የገበያ ማዕከላት ግንባታ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- በሚቀጥሉት አምስት አመታት በወረቀት የሚካሔዱ አሰራሮችን በማስቀረት የዲጂታል ቴክኖሎጂ ግብይትና አገልግሎት በተሻለ ...
Feb 8, 2025