🔇Unmute
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በምግብ ዋስትና እና በኢኮኖሚ ልማት ዘርፍ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራት ለመላው አፍሪካ አገራት ትልቅ አርአያ ናቸው ሲሉ የላይቤሪያ ከፍተኛ የልዑካን ቡድን አባላት ገለፁ።
ልዑኩ ዛሬ፣ የግብርና እና የሌማት ትሩፋት ስራዎች፣ ዘመናዊ መስኖን መሰረት ያደረገ የከተማ ግብርና እንዲሁም የእንስሳትና የዶሮ እርባታ ልማት ሥራዎችን በቢሾፍቱ የመስክ ምልከታ አድርጓል።

የላይቤሪያ ፕሬዝዳንት የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ሳሙኤል ኮፊ ዉድስ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን እና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየተከተለች ያለው መንገድ እጅግ ተራማጅ ነው።
ላይቤሪያም የኢትዮጵያን ተሞክሮ በመቅሰም ዩኒቨርሲቲዎቿን፣ ወጣቶችን እና ማህበረሰቡን በስፋት በማሳተፍ ለምግብ ምርትና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ የግብርና ውጤቶችን ለማሳደግ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላት አረጋግጠዋል።
በተለይም በግብርናው ዘርፍ የታየው የወጣቶች ተሳትፎ በአፍሪካ ለሚታየው የስራ አጥነት ችግር ትልቅ መፍትሄ መሆኑን ገልጸዋል።
ወጣቶች ትኩረታቸውን ከቢሮ ስራ ወደ ግብርና በማዞር የወደፊት ህይወታቸው ለመዘጋጀት የሚያደርጉት ጥረት ለጠቅላላው አፍሪካ ወሳኝ ትምህርት የሚሰጥ መሆኑንም አብራርተዋል።
በጉብኝታቸው ወቅት ከተመለከቷቸው የኢትዮጵያ እርሻ ውጤቶችና ከታየው ተነሳሽነት ትልቅ ልምድ መቅሰማቸውንም አረጋግጠዋል።

የላይቤሪያ የኢንፎርሜሽን ምክትል ሚኒስትር ዳንኤል ኦ. ሳንዶ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በምግብ ዋስትና እና በኢኮኖሚ ልማት ዘርፍ እያከናወነች ያለው ተግባር ለመላው አፍሪካ አርአያ የሚሆን ነው ብለዋል።
ሚኒስትሩ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጋር በተካሄደው ውይይት፤ ኢትዮጵያ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ የምግብ ዋስትናን የቀዳሚነት አጀንዳዋ አድርጋ መነሳቷን መረዳታቸውን ጠቁመዋል።
ራሷን መመገብ የማትችል ሀገር መሰረቷ ደካማ ነው ያሉት ሚኒስትሩ፤ ኢትዮጵያ በዚህ ረገድ የጀመረችው ተራማጅ የዕድገት ጎዳና የሚደነቅ መሆኑን ተናግረዋል።
ሚኒስትሩ በጉብኝታቸው ወቅት በኢትዮጵያ በመስኖ ቴክኖሎጂ የታገዘ የግብርና ሥራ መከናወኑና በዚህም በርካታ ሴቶችና ወጣቶች ተጠቃሚ መሆናቸውን አንስተዋል።
ኢትዮጵያ የውጭ ምርትን በመቀነስና የግብርና ምርቶቿን ወደ አውሮፓ ገበያ በመላክ የንግድ ሚዛኗን ለማስተካከል የምታደርገውን ጥረትም አድንቀዋል።
ሀገራቸው በምግብ ራሷን እንድትችል ለማድረግ የኢትዮጵያን ተሞክሮ መውሰድ እንደሚፈልጉም አክለዋል።

የላይቤሪያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ሌይሊ ፊሊፕስ ማፓርየን (ዶ/ር) ፣ እዚህ ያየሁት የግብርና ኢንዱስትሪ የዳበረና የአገሪቱን ልማት በብቃት እየደገፈ መሆኑን ተረድቻለሁ ብለዋል።
የኢትዮጵያ ቆይታዬ ወደ ላይቤሪያ ይዤው የምመለሰው ብዙ ትምህርት ሰጥቶኛል ያሉት የላይቤሪያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት፤ ጉብኝቱ በላይቤሪያ ዩኒቨርሲቲ ያለውን የግብርና ፕሮግራም እንዴት ማዘመን እነደሚቻል እንዳስብ አድርጎኛል ብለዋል።
የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ በሰጡት ማጠቃለያ፤ ኢትዮጵያ ጸጋዎቿን በመጠቀምና በማቀናጀት ያከናወናቸው የልማት ተግባራት ለአፍሪካውያን ምሳሌ እንደሚሆኑ የልዑካን ቡድኑ እንዳነሱላቸው ገልጸዋል።

በቀጣይ የላቤሪያ የግብርና ሳይንቲስቶችና ተመራማሪዎች ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመጡ ጠቁመዋል።
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በምግብ ዋስትና እና በኢኮኖሚ ልማት ዘርፍ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራት ለመላው አፍሪካ አገራት ትልቅ አ...
Apr 16, 2026
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ለውጡ የሀገሪቱን ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ስብራቶች በመጠገን፣ ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ከፍታና ለማህበራዊ ትስስ...
Apr 3, 2026
ቦንጋ ፤የካቲት 16/2017 (ኢዜአ) ፡-በቦንጋ ከተማ የተካሄደውን የህዝብ ውይይት የመሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች በከተማው የተለያዩ የልማት ...
Feb 24, 2025
ደብረብርሀን፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ገበያን ለማረጋጋት የሚያግዙ ከአንድ ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የገበያ ማዕከላት ግንባታ...
Feb 24, 2025