
ደሴ፤ ሀምሌ 16/2017 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ወሎ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 57 የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታቸው ተጠናቆ ለመጪው በጋ አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ መደረጋቸውን የዞኑ መስኖና ቆላማ አካባቢዎች ልማት መምሪያ አስታወቀ።
ከ57ቱ የመስኖ ፕሮጀክቶች ውስጥ 43ቱ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ግንባታቸው ተጀምሮ የተጠናቀቁ መሆናቸውም ተጠቁሟል።

የመምሪያው ኃላፊ አቶ ተክሉ ጥላሁን ለኢዜአ እንደገለፁት በዞኑ የውሃ አማራጮችን በመጠቀም አርሶ አደሩ ምርታማነቱን ማሳደግ እንዲችል የመስኖ ፕሮጀክት ግንባታው ተጠናክሮ ቀጥሏል።
በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ972 ሚሊዮን ብር 57 የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማስገንባት ለመጪው የበጋ መስኖ ልማት ዝግጁ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል።
ከፕሮጀክቶቹ ውስጥም 43ቱ በ2017 በጀት ዓመት ግንባታቸው ተጀምሮ በበጀት ዓመቱ የተጠናቀቁ ሲሆን ቀሪዎቹ ባለፉት ዓመታት የተጀመሩ እንደነበሩ አስታውሰዋል።

የተገነቡት ፕሮጀክቶችም ከ6 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከ11 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በመስኖ ልማት ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚችሉም ተናግረዋል።
በዞኑ በዓመት እስከ ሶስት ጊዜ በማምረት የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥና ገበያውን ከማረጋጋት ባለፈ ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገውን ጥረት የሚደግፉ ናቸው ብለዋል።
የመስኖ ፕሮጀክቶቹ ግንባታ ከተከናወነባቸው መካከል ደሴ ዙሪያ ወረዳ፣ አልብኮ፣ ቦረና፣ መቅደላ፣ ተንታ፣ ለገሂዳና ሌሎች ወረዳዎች እንደሚገኙበትም ጠቅሰዋል።
አርሶ አደሩም ፕሮጀክቶቹን በመጠበቅና በመንከባከብ ለረጅም ጊዜ አገልግሎት እንዲሰጡ በማድረግ ዘላቂ ተጠቃሚነቱን እንዲያሳድግ አሳስበዋል።
በደሴ ዙሪያ ወረዳ የቀበሌ 40 ነዋሪ አርሶ አደር ሰይድ አራጋው በበኩላቸው ዘንድሮ በተገነባላቸው የመስኖ ፕሮጀክት አንድ ሄክታር የሚጠጋ መሬታቸውን በበጋ ስንዴና በቋሚ ፍራፍሬ ለማልማት ተዘጋጅተዋል።

ቀደም ሲል በባህላዊ መስኖ አትክልት ለማልማት ቢሞክሩም ተጠቃሚ መሆን ሳይችሉ መቅረታቸውን ጠቁመው የዘመናዊ መስኖ መገንባቱ ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን እንደሚያረጋግጥላቸውም ተናግረዋል።
ሌላው የመቅደላ ወረዳ 04 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አብዱራህማን የሱፍ በሰጡት አስተያየት ዘንድሮ በተገነባላቸው የመስኖ ፕሮጀክት ግማሽ ሄክታር ማሳቸውን በበጋ ስንዴ ለማልማት ተዘጋጅተዋል።

መንግስት የዓመት ዝናብን ሳንጠብቅ በዘመናዊ መስኖ ምርታማነታችንን በማሳደግ ተጠቃሚ መሆን እንድንችል ምቹ ሁኔታ በመፍጠሩም እናመሰግናለን ብለዋል።
በደቡብ ወሎ ዞን በ2016 በጀት ዓመት በተገነቡ 18 የመስኖ ፕሮጀክቶች ከ3 ሺህ የሚበልጡ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም ከመምሪያው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ሀዋሳ፣ ነሐሴ20/2018 (ኢዜአ)፡-በሀዋሳ ከተማ የተጀመሩ የሐይቅ ዳርቻ እና የኮሪደር ልማት ሥራዎችን በተያዘላቸው ጊዜ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ...
Aug 27, 2026
ሐረሪ ፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል የኢንቨስትመንት ፍቃድ እና መሬት ወስደው ወደ ግንባታና ማምረት ባልገቡ 12 ባለሀብቶች ላይ የኢንቨስትመንት...
Aug 14, 2026
ደሴ፤ነሐሴ 6/2018(ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ173 ሺህ ለሚበልጡ አርሶ አደሮች የሁለተኛ ደረጃ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ደብተር መሰጠ...
Aug 13, 2026
ባሕር ዳር ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ መቻሉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር...
Jul 31, 2026