🔇Unmute
ጎንደር፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ቀደም ሲል የለሙ ተፋሰሶች ለሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በፈጠሩት ምቹ መደላድል ተጠቃሚ መሆናቸውን አርሶ አደሮች ተናገሩ።
የዞኑ አርሶ አደሮች በመርሃግብሩ ታግዘው በንብ ማነብ፣ በወተት ላም እርባታ፣ በእንስሳት ማድለብ እንዲሁም በአቮካዶ ተክልና በቡና ልማት በመሰማራት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ተናግረዋል፡፡
በዞኑ የላይ አርማጭሆ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር እሸቴ ንብረት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት በተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ ባገገሙ ተፋሰሶች በቡና ልማት ተሰማርተው ከምርት ሽያጭ በዓመት እስከ 80ሺህ ብር ገቢ እያገኙ ነው፡፡

ያገገሙ ተፋሰሶች ለአርሶ አደሩ የሀብት ምንጭ እየሆኑ መጥተዋል ያሉት አርሶ አደሩ ለልጆቻችን ጭምር የሥራ ዕድል በመፍጠር በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንድንሆን አስችሎናል ብለዋል፡፡
የአለፋ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር በላይ መንግስቴ በበኩላቸው፤ በሌማት ትሩፋት መርሃግብር በንብ ማነብ ሥራ ተሰማርተው አሁን ላይ ከ40 የንብ ቀፎዎች ማር እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

በለሙ ተፋሰሶች እያከናወኑት ባለው የንብ ማነብ ሥራ ከአንድ የንብ ቀፎ እስከ 15 ኪሎ ግራም ማር በመሰብሰብና አንዱን ኪሎ በ600 ብር በመሸጥ ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የገለጹት።
በለሙ ተፋሰሶች በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የወተት ላም እርባታ ሥራ መጀመራቸውን የገለጹት ደግሞ በጎንደር ዙሪያ ወረዳ የምንዝሮ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር በሪሁን ታከለ ናቸው፡፡

ተፋሰሱ ለእንስሳት መኖ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንና ካሏቸው ሦስት የወተት ላሞች በቀን የሚያገኙት 24 ሊትር ወተት ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ በበኩላቸው፤ ባለፉት ተከታታይ ዓመታት በህብረተሰቡ ተሳትፎ በተከናወነ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራ የለሙ አካባቢዎች ለዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሪያና የሀብት ምንጭ እየሆኑ ነው፡፡

የለሙ ተፋሰሶች ለሌማት ትሩፋት መርሀግብር ትግበራ ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውን ጠቁመው፣ በዚህም አርሶ አደሩ የምግብ ሉአላዊነቱን እንዲያረጋግጥና ሀብት እንዲያፈራ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል።
ያለፉትን ዓመታት ተሞክሮ በመቀመር በዘንድሮ የበጋ ወራት በዞኑ 15 ወረዳዎች የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት መጀመሩን የተናገሩት ሃላፊው በዚህም 52 ሺህ ሄክታር የሚሸፍን የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ ይከናወናል ሲሉ ገልጸዋል።
እንደ አቶ ንጉሴ ገለጻ ለ35 ተከታታይ ቀናት በሚካሄደው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ ከ467 ሺህ በላይ ነዋሪዎች በልማት ቡድኖች ተደራጅተው ይሳተፋሉ።
አሶሳ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ):- ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የትውልዱ አሻራና ኩራት ነው ሲሉ የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አብዱልሙህሲን ሐሰን...
Feb 28, 2025
ሚዛን አማን፤የካቲት 20/2017 (ኢዜአ)፦በቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ከተማ በማህበር ተደራጅተው በተለያዩ የሥራ ዘርፎች የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች ውጤታማ በመ...
Feb 28, 2025
አዲስ አበባ፤የካቲት 4 /2017(ኢዜአ)፦ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በግብርናው ዘርፍ እያከናወነ ያለው በምርምር የተደገፈ ስራ ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ የሕዝብ ተወካዮች ም...
Feb 12, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- የቦንጋ የተቀናጀ የግብርና ግብዓትና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ማዕከል መገንባት በክልሉ ለግብርና ስራው መሠረታዊ የሆነ...
Feb 8, 2025