አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2017(ኢዜአ)፡- ወደ ትግበራ ምዕራፍ የገባው የናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ሁሉንም የተፋሰሱን ሀገራት ያካተተ የውሃ ሀብት ልማት ትብብር የሚፈጥር መሆኑን የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር ኢ/ር) ገለጹ።
ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ እና አፍሪካ ህብረት የጀርመን አምባሳደር ሀንስ ሀንፊልድን ዛሬ በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።
በውይይቱ ወቅት ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ንጹህ አረንጓዴ ኢነርጂ በማምረት ቀጣናውን በኃይል ለማስተሳሰር እያከናወነች ያለው ስራ ውጤታማ መሆኑን ገልጸዋል።
በስድስት ሀገራት ፀድቆ ወደ ስራ የገባው የናይል ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ሁሉም የተፋሰሱ ሀገራትን አሳታፊ ያደረገ የውሃ ልማት ትብብር ለመፍጠር እንደሚያስችልም አመልክተዋል።
በሌላ በኩል በውሃ ሀብት ልማት በተከናወኑ ስራዎች ከ74 ሚሊዮን በላይ ዜጎችን የንጹህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ነው ሚኒስትሩ የጠቆሙት።
የጀርመን መንግስት በኢነርጂ ልማት ዘርፍ፤ በንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትና በውሃ ሀብት አስተዳደር ዘርፍ ድጋፍ እንደሚያርግ ጠቅሰው፤ በተለይ ጂአይዜድ በገጠር የሀገሪቱ ክፍል ኤሌኬትሪክ ለማዳረስ ለረጅም ጊዜ ድጋፍ ሲያደርግ መቆየቱን አንስተዋል።
በቀጣይም ከዋና የሀይል መስመር ርቀው የሚገኙ ገጠራማ አካባቢዎችን የኦፍግሪድ ኤሌክትሪክ ተጠቃሚ ለማድረግ ድጋፍ እንዲያደርጉም ጠይቀዋል፡፡
በኢትዮጵያ እና አፍሪካ ህብረት የጀርመን አምባሳደር ሀንስ ሀንፊልድ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በታዳሽ ኃይል ልማት ላይ አበረታች ስራ እያከናወነች መሆኑን ገልጸው የቀጣናዊ የኃይል ትስስሩ ዘርፈ ብዙ ትብብርን እንደሚፈጥርም አመልክተዋል።
በሌላ በኩል አምባሳደሩ በኢትዮጵያ ጠንካራ የኢኮኖሚ ሪፎርም እየተደረገ መሆኑን መግለጻቸውን ከውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።