አዲስ አበባ፤ የካቲት 10/2017(ኢዜአ)፡- ስምንተኛው የአፍሪካ የቢዝነስ ፎረም በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።
ፎረሙ የሚካሄደው “ከእመርታ ወደ ብልጽግና፤ የአፍሪካን ቀጣናዊ የእሴት ሰንሰለቶች አቅም ማጠናከር” በሚል መሪ ሃሳብ ነው።
በፎረሙ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ፣ የመንግሥት ተቋማት፣ የግሉ ዘርፍ ተዋናዮች፣ የልማት ድርጅቶች፣ የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች፣ የፋይናንስ ተቋማትን ጨምሮ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ተወካዮች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
የቢዝነስ ፎረሙ በአፍሪካ የቁም እንስሳት፣ ግብርና እና ፋርማሲዩቲካል ዘርፎች ቀጣናዊ የእሴት ሰንሰለት እና ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖች ልማት ላይ እንደሚያተኩር ተጠቁሟል፡፡
መንግስታት፣ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ማህበረሰቦች፣ የፋይናንስ ተቋማት እና የግሉ ዘርፍ በአፍሪካ እሴትን በመጨመር፣ በዘላቂ የኢንዱስትሪ ልማት፣ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ አጠቃቀም፣ በስራ እድል ፈጠራ እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እያከናወኑት ባለው ስራ ዙሪያ ውይይት ይደረጋል።
ፎረሙ ለቀጣናዊ እሴት ሰንሰለት እና ልዩ ኢኮኖሚ ዞኖች ልማት የኢንቨስትመንት ሀብት ማሰባሰብ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይም ይመክራል ተብሏል።
ፎረሙን በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከአፍሪካ ፋይናንስ ኮርፖሬሽን እና ከአረብ ባንክ ፎር ኢኮኖሚክ ዴቨሎፕመንት ጋር በመተባበር እንዳዘጋጁት ተገልጿል።
የአፍሪካ የቢዝነስ ፎረም እ.አ.አ ከ2018 ጀምሮ መየዓመቱ በመካሄድ ላይ ይገኛል።
ፎረሙ መንግስታት፣ ባለሀብቶች፣ ፕሮጀክት አስተባባሪዎች እና ባለድርሻ አካላት በዘላቂ ልማት ግቦች፣ የአጀንዳ 2063 ውጥኖችን ለማሳካት ባሉ እድሎች፣ ፈተናዎች እና ተግባራዊ ምላሾች ላይ እንዲወያዩ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ኮሚሽኑ ገልጿል።