ሮቤ፤ የካቲት 10/2017(ኢዜአ)፡- የሮቤ ከተማን ለነዋሪው ምቹና የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የተጀመረው የኮሪደር ልማት ስኬታማ እንዲሆን ሁለንተናዊ ድጋፍ እንደሚያደርጉ የከተማው ነዋሪዎች ገልጸዋል።
በሮቤ ከተማ በመጀመሪያው ምዕራፍ የ7 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ከተማ አስተዳደሩ ገልጿል።
የሮቤ ከተማ የኮሪደር ልማትን በማስመልከት ኢዜአ ከነዋሪዎችና የአስተዳደር አካላት ጋር ቆይታ ያደረገ ሲሆን ነዋሪዎቹም ስራውን እንደሚያግዙ አረጋግጠዋል።
ከከተማው ነዋሪዎች መካከል ሐጂ ቃሲም ኡስማን እንዳሉት የኮሪደር ልማቱ ከተማችንን በማዘመን ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ ያደርጋታል።
አስተዳደሩ ከተማችንን በማዘመን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ እያከናወነ ለሚገኘው የኮሪደር ልማት ስኬታማነት ድጋፋችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል።
በአሁኑ ወቅት የተጀመረው የኮሪደር ልማት የከተማዋን የቱሪዝምና የንግድ ማዕከልነት የሚያጠናክር ነው ሲሉም ገልጸዋል።
የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገፅታ ከመቀየርና ለኑሮ ተስማሚ አካባቢን ከመፍጠር ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል የሚፈጥር ፕሮጀክት መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ሌላው የከተማ ነዋሪ ከድር ከማል ናቸው።
የተጀመራው ልማት በአግባቡ ተጠናቆ ከተማዋ ለኑሮ ምቹና ተስማሚ እንድትሆን ከመንግሥት ጎን በመሰለፍ የሚጠበቅብንን ድጋፍ እናደርጋለን ያሉት ደግሞ አቶ ሐይሉ መንግስቱ ናቸው።
የሮቤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዲኖ አሚን በበኩላቸው የሚከናወነው የኮርደር ልማት የከተማውን ማስተር ፕላን መሠረት አድርጎ መሆኑን ተናግረዋል።
በዚህም የእግረኛና የብስክሌት መንገድ፣ የአረንጓዴ መዝናኛ ቦታዎችንና ሌሎች መሠረተ ልማቶችን በማቀናጀት የሚተገበር መሆኑን ገልጸዋል።
በከተማው የመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ልማት ከ7 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር በላይ ርዝመት ያላው ዋና ዋና መንገዶችን ማልማትና ማስዋብ ስራም በቅርቡ ይጀመራል ብለዋል።
በእስከአሁኑ ሂደት ህብረተሰቡ ንብረቱን በፍላጎቱ ከመንገድ ዳር ማንሳቱን ጠቁመው ሌሎች የኢትዮ-ቴሌኮምና የኤሌክትሪክ መስመር ፖሎችን ከመንገድ ዳር የማንሳት ሥራ እየተከናወነ ነው ብለዋል።
የኮሪደር ልማቱ ከተማዋን ለነዋሪ ምቹና ውብ ከማድረግ ባለፈ ለንግድና ኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ተመራጭ ማድረግ የሚያስችል መሆኑን አብራርተዋል።
የኮሪደር ልማቱን በእቅዱ መሰረት በሚቀጥሉት ሦስት ወራት በጥራት ለማጠናቀቅ የውስጥ ገቢን አሟጦ መሰብሰብና መንግሥት ለሥራው የመደበውን የካፒታል በጀት በማቀናጀት በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል።