ወልቂጤ፤ የካቲት 17/2017(ኢዜአ)፦ በየአካባቢው ያሉ ፀጋዎችን በማልማት የሕዝብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተከናወኑ ሥራዎች ስኬታማ መሆናቸውን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ።
በብልጽግና ፓርቲ ሁለተኛ መደበኛ ጉባኤ ውሳኔዎችና አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ ሕዝባዊ ውይይት መድረክ በወልቂጤ ከተማ እየተካሄደ ነው።
በውይይቱ ላይ የተገኙት ሚኒስትሯ ብልጽግና ፓርቲ እንደ ሀገር ያሉ ፀጋዎችን በማልማት የሕዝብን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መምጣቱን ገልጸዋል።
በፓርቲው ሁለተኛ መደበኛ ጉባኤ የተቀመጡ ትውልድ ተሻጋሪ አቅጣጫዎችን ለማስፈጸም ይሰራል ያሉት ወይዘሮ ጫልቱ ለተግባራዊነቱ ህዝብን ከማሳተፍ ባለፈ ለዘላቂ ሰላምና ልማት ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል።
በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በየዘርፉ በተከናወኑ ሥራዎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ እያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል።
ለዚህም የወልቂጤ ከተማ በሥራ ዕድል ፈጠራ እና በመሰረተ ልማት ዝርጋታ እየተከናወኑ ያሉት የልማት ሥራዎች የነዋሪውን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ መሆናቸውን በማሳያነት ጠቅሰዋል።
የከተማዋ ሁለንተናዊ ልማት እየጎለበተ እንዲሄድ ገቢን በአግባቡ አሟጦ መሰብሰብ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
የወልቂጤ ከተማ ከንቲባ አቶ ሙራድ ከድር አስተዳደሩ ነዋሪውን በማሳተፍ የሚያከናውናቸው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል።
በማህበራዊ ጉዳይ ህዝብን በማሳተፍ ለአቅመ ደካሞች የመኖሪያ ቤቶች የመስራትና የማደስ ሥራ በማከናወን በርካቶችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል።
በኢኮኖሚ ዘርፍም የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰሩ ሥራዎች ውጤት እየተመዘገበ መምጣቱን ገልጸው ኢንቨስትመንትን በማስፋፋት ዜጎች በሥራ ዕድሉ ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉንም ጠቅሰዋል።
ህዝባዊ መድረኩ እነዚህን ተግባራት የበለጠ ለማጠናከርና የጋራ አረዳድን ለማምጣት አጋዥ መሆኑንም ተናግረዋል።