አሶሳ፤ የካቲት 17/2017(ኢዜአ):- በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ያለውን እምቅ ሃብት በማልማት የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተደረገ ያለው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ ተናገሩ።
በአሶሳ ዞን ዑራ ወረዳ በኦሮሚያ ክልል መንግሥት ድጋፍ የተገነባውን የባሮ ኢፈ ቦሩ ትምህርት ቤት የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ እና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሐሰን ተመርቋል።
በተመሳሳይ በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል አሶሳ ከተማ በግል ባለሃብት የተገነባው የምግብ ዘይት ፋብሪካም ተመርቆ ስራ ጀምሯል።
ከዚሁ መርሃ ግብር በኋላ መልዕክት ያስተላለፉት አቶ ሽመልስ አብዲሳ፤ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ያለውን እምቅ ሃብት በማልማት የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተደረገ ያለው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን ገልጸዋል።
ለአልሚ ባለሃብቶች በክልሉ በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች መሳተፋቸውም የሚበረታታ ነው ብለዋል።
ከዚሁ መርሃ ግብር በተጨማሪ በአሶሳ የተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር የሌማት ትሩፋት ስራዎችንም ጎብኝተዋል።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሐሰን በክልሉ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል።
በክልሉ ገና ያልተነካ እምቅ ሃብት በመኖሩ ባለሃብቶች በተለያዩ የልማትና ኢንቨስትመንት መስኮች ቢሳተፉ ተጠቃሚ እንደሚሆኑም አንስተዋል።
በዛሬው እለት የተመረቀው የምግብ ዘይት ፋብሪካም ለዚሁ ጥሩ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው የግብርና ምርቶችን በማቀነባበር እሴት ጨምሮ ለገበያ ማቅረብ የሚያስችል ነው ብለዋል።
በክልሉ ያለውን እምቅ ሃብት በማልማት ህዝቡ ተጠቃሚ እንዲሆን የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠው በክልሉ መስራት የሚፈልጉ ባለሃብቶችን ለመቀበል ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁነት መኖሩንም አረጋግጠዋል።
የፋብሪካው ባለቤት ወይዘሮ ሮማን ፍቃዱ፤ ክልሉ ላደረገላቸው ትብብር አመስግነው በቀጣይም በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ለመሰማራት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።
የምግብ ዘይት ፋብሪካው በ150 ሚሊዮን ብር የተገነባ ሲሆን የኑግ ምርትን በመጠቀም በብዛት ዘይት በማምረት ለአካባቢው ገበያና ለአጎራባች ክልሎች ጭምር ማቅረብ የሚያስችል መሆኑ ገልጸዋል።
የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ በአሶሳ የሌማት ትሩፋት ስራዎችንም ተመልክተዋል።
#Ethiopia