አዲስ አበባ ፤ የካቲት 18/2017(ኢዜአ)፦ የፌደራል ቤቶች ኮርፖሬሽን የመንግስት እና የግል አጋርነትን መፍጠርን ጨምሮ ለቤቶች ልማት የሚያስፈልገውን አማራጭ የፋይናንስ ምንጮች በጥናት መለየቱን አስታወቀ።
በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲግንስ ስር ያሉ ተቋማት የግማሽ ዓመት የስራ አፈጻጸም ግምገማ መካሄዱን እንደቀጠለ ነው።
የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን የስድስት ወራት አፈጻጸም ቀርቦ ግምግማ ተደርጎበታል።
ኮርፖሬሽኑ በገቢ አሰባሰብ፣ በቤት አቅርቦት፣ የቤቶች ጥገና እና ለግንባታዎች አስፈላጊውን ፋይናንስ በመመደብ ረገድ የላቀ አፈጻጸም ማስመዘገቡ ተመላክቷል።
በግምገማው እንደቀረበው ኮርፖሬሽኑ አፈጻጸሙን ይበልጥ ለማላቅ የንብረት እና ሀብት አስተዳደር አቅሙን ለማሳደግ እቅድ ይዟል።
ለዚህም የኪራይ ሊዝ ስምምነቶች እና የውል አስተዳደር ላይ ትኩረቱን አድርጎ እንደሚሰራ ገልጿል።
በተጨማሪም ኮርፖሬሽኑ በቀጣይ ስድስት ወራት ትኩረት የሚያደርግባቸው የስትራተጂ ትኩረት አቅጣጫዎችንም ለይቷል።
በሪል ስቴቶች ውስጥ ገቢ አመንጪ የሆኑ ንብረቶችን በባለቤትነት መያዝ እና ማስተዳደር፣ የመንግስት እና የግል አጋርነት እንዲሁም ሽርክናን ጨምሮ ለቤቶች ልማት የሚያስፈልጉ አማራጭ የፋይናንስ ሀብቶችን ማፈላለግ ላይ በትኩረት ለመስራት ማቀዱን ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲግንስ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።