አዲስ አበባ ፤ የካቲት 18/2017(ኢዜአ)፦ውስብስብና ዓለም አቀፍ ችግሮችን ለመፍታት የተለወጠ የዓለም ስርዓት ያስፈልጋል ሲሉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዢ ማሞ ምህረቱ ገለጹ።
የብሪክስ አባል ሀገራት ዋና አስተባባሪዎች እና ምክትል አስተባባሪዎች (ሼርፓስ እና ሱስ ሼርፓስ) የ2025 የመጀመሪያ ስብስባ ዛሬ በብራዚል መዲና ብራዚሊያ መካሄድ ጀምሯል።
በአቶ ማሞ ምህረቱ የተመራው የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን በስብስባው ላይ እየተሳተፈ ነው።
በስብስባው መክፈቻ ላይ የብራዚል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማውሮ ቪዬራ የመክፈቻ ንግግር አድርገዋል።
በብሪክስ የኢትዮጵያ ዋና አስተባባሪ (ሼርፓ) አቶ ማሞ ምህረቱ ኢትዮጵያ ለረጅም ዘመናት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ስርዓትን ማዕከል ባደረገ መልኩ ለባለብዙወገን ትብብር እና ለጋራ ደህንነት ድጋፍ ማድረጓን ገልጸዋል።
ለዓለም በርካታ እና ውስብስብ ፈተናዎች መፍትሄ የሆኑ እርምጃዎችን ለመውሰድ የዓለም ስርዓት ከወቅቱ ጋር የሚሄድ ማሻሻያ እንደሚያስፈልገው አመልክተዋል።
አቶ ማሞ ኢትዮጵያ የአዲሱ ልማት ባንክ አባል መሆን በ2025 ቁልፍ የትኩረት መስኮች አንዱ መሆኑን ነው የገለጹት።
በብሪክስ ሀገራት መካከል ያለው የንግድ ግንኙነት አድማስ እንዲሰፋ መስራት እንደሚገባም አመልክተዋል።
በብሪክስ ማዕቀፍ ውስጥ ያሉ ግቦች፣ ፕሮግራሞች እና ኢኒሼቲቮች ትግበራ ውጤታማነት በቁርጠኝነት መስራት እንደሚገባም ተናግረዋል።
በውይይቱ ላይ ኢትዮጵያ ብራዚል በ2025 የብሪክስ ፕሬዝዳንቷ ትኩረት ሰጥታ የምትሰራባቸውን ቁልፍ ጉዳዮች እንደምትደግፍ ገልጻለች።
የዓለም ጤና፣ የዓለም አስተዳደር ስርዓት ማሻሻያ፣ የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ፣ የሰው ሰራሽ አስተውሎት አስተዳደር፣ የደቡባዊ ንፍቀ ክበብ ትብብር እና የብሪክስ የተቋማት ልማት የትኩረት መስኮቹ ናቸው።
የብሪክስ አባል ሀገራት ዋና አስተባባሪዎች እና ምክትል አስተባባሪዎች ስብስባ ለሁለት ቀናት እንደሚቆይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።