ደብረ ማርቆስ ፤የካቲት 24/2017(ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን በስድስት ወራት ከአንድ ነጥብ ሁለት ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን የዞኑ ገቢዎች መምሪያ ገለጸ።
የመምሪያው ሃላፊ ተወካይ አቶ ግዛቸው ወንድሜነህ ለኢዜአ እንደገለጹት ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ለልማት ለማዋል እየተሰራ ይገኛል።
በዚህም በበጀት ዓመቱ ከተለያዩ የገቢ አርስቶች 3 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ በግማሽ ዓመቱ ብቻ ከ1 ቢሊየን 284 ሚሊየን ብር በላይ ገቢ ተሰብስቧል።
ይህም ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ21 በመቶ በላይ ብልጫ እንዳለው ጠቁመዋል።
ለግብር አሰባሰቡ ስኬታማነት ቅንጅታዊ አስራርን መዘርጋትና የማህበረሰቡ ግብርን በወቅቱ የመክፈል ባህል እያዳበረ በማምጣቱ የመጣ ለውጥ መሆኑን አስረድተዋል።
ከግብር ከፋዮች መካከል የደብረ ወርቅ ከተማ ነዋሪው አቶ ይርጋለም ተኮላ እንደገለጹት ከንግድ ስራቸው ካገኙት ገቢ የመንግስትን ገቢ በወቅቱ ከፍለዋል።
መንግስት ለልማትና ለአገልግሎቶች የሚያውለው ወጪ በሚሰበስበው ገቢ የሚሸፈን መሆኑን በመገንዘባቸው ግብራቸውን በወቅቱ ለመክፈል እንዳነሳሳቸው ተናግረዋል።
''በሰራሁት ልክ ግብር እየከፈልኩ ለአገሬ እድገት የበኩሌን እወጣለሁ'' ያሉት ደግሞ የሉማሜ ከተማ አስተዳደር ነዋሪ አቶ ቢምረው ገሌ ናቸው።
በግንባታ እቃዎች ሽያጭ በመሰማራት ካገኙት ገቢ ላይም 210 ሺህ ብር ለመንግስት በመክፈል የዜግነት ግዴታቸውን እንደተወጡ አስረድተዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን የመደበኛና የከተማ አገልግሎት ግብር የሚከፍሉ ከ42 ሺህ በላይ ነጋዴዎች መኖራቸውን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።