አዲስ አበባ፤ መጋቢት 01/2017(ኢዜአ)፦ በዘመኑ አርበኝነት በራሳችን ክህሎት የበለጸገች ኢትዮጵያን ማነጽ እንደሚቻል የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ።
የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት አዘጋጅነት "ኢትዮጵያ እያሸነፈች ትሻገራለች" በሚል መሪ ሃሳብ "ክህሎት ስለ ኢትዮጵያ" ምዕራፍ ሁለት የምክክር መድረክ በመካሄድ ላይ ይገኛል።
የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ለመድረኩ መነሻነት የተሰናዳውን የኢንዱስትሪ፣ የስራ ዕድል ፈጠራና የክህሎት ልማት ተግባራትን የሚያሳይ የፎቶ አውደ ርዕይ መርቀው ከፍተዋል።
በዚሁ ወቅት በራሳችን ክህሎት የበለጸገች ኢትዮጵያን ማነጽ እንችላለን ብለዋል።
ክህሎት ስለ ኢትዮጵያ መድረክ የቀደምት ኢትዮጵያዊያን የአርበኝነት ተጋድሎ የቅኝ አገዛዝ እሳቤን ድል በነሱበት የየካቲት ወር ማግስት መዘጋጀቱ ልዩ እንደሚያደርገው ገልጸዋል።
የአሁኑ ትውልድም ቅድመ አያቶቹ ከአራቱም ማዕዘናት በዓድዋ ተራሮች ተመው ለጥቁር ህዝቦች ሁሉ የነፃነት ቀንዲል ከሆኑበት የአርበኝነት የድል ታሪክና ወኔ በመላበስ በትጋት መስራት እንደሚኖርበት አስገንዝበዋል።
በዚህም በቅድመ አያቶች የነፃነት የድል ታሪክ የጸናችውን ኢትዮጵያ ክህሎት ታጥቀን በዘመኑ አርበኝነት የበለጸገች ኢትዮጵያን ማነጽ እንችላለን ብለዋል።
ሁለተኛ ምዕራፍ የመጀመሪያው ዙር "ስለኢትዮጵያ" መድረክ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቡታጅራ ከተማ ሁለተኛው ዙር ደግሞ በሐረር ከተማ መካሄዱ ይታወሳል።
ክህሎት ስለ ኢትዮጵያ ሁለተኛ ምዕራፍ መድረክ ላይ በቀረበ የመነሻ ጽሁፍ ምክክር እየተደረገበት ይገኛል።