ሐረር፤ መጋቢት 7/2017(ኢዜአ)፡- የሐረር በርን ለዓለም ህዝብ የሚያስተዋውቅ በአረንጓዴ መብራት የማድመቅ ፕሮጀክት በአየርላንድ መንግስት አማካኝነት ተከናወነ።
በሥነ ስርዓቱ ላይ የተገኙት በኢትዮዽያ የአየርላንድ ኤምባሲ ቆንስላ ስቴፈን ፍሬን እንደተናገሩት የአየርላንድ መንግስት ባህላዊና ታሪካዊ ቅርሶችን ለዓለም የማስተዋወቅ ስራ እያከናወነ ነው።
በአየርላንድ መንግስት የሚደገፈው ዓለም አቀፉ የአረንጓዴ መብራት ፕሮጀክት የሐረር በር በምሽት በአረንጓዴ መብራት በማድመቅ ያለውን መስህብ ለዓለም ህዝብ ማስተዋወቅ ነው።
ፕሮጀክቱ ከዚህ በፊት የላሊበላውን ቤተ ጊዮርጊስ እና የፋሲል ግንብን የመሳሰሉ ቅርሶችን እንዲሁም ሌሎች ተቋማትን በምሽት በአረንጓዴ መብራት በማድመቅ ለዓለም ህዝብ እንዲተዋወቁ አድርጓል።
ዘንድሮም የሀረር በርን በአረንጓዴ መብራት እንዲደምቅ በማድረግ የማስተዋወቅ ስራ ተከናውናል ብለዋል።
የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ አቶ እሸቱ አሰፋ ለኢዜአ እንደገለጹት የአረንጓዴ መብራትን የማድመቅ ፕሮግራም የቱሪዝም መዳረሻዎችን በዘላቂነት በማጎልበት የማስተዋቅ ተግባር ነው።
ይህም መዳረሻዎቹን ለመላው ዓለም በማስተዋወቅ ጎብኚዎች ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ የማድረግ ዓላማ እንዳለው ገልጸዋል።
ከዚህ ቀደምም በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ ታሪካዊና ጥንታዊ ቅርሶችን በአረንጓዴ መብራት በማድመቅ የተከናወነው የማስተዋወቅ ስራ ቅርሶቹ በዓለም ላይ ደምቀው እንዲታዩ ማስቻሉን ተናግረዋል።
በሐረሪ ክልል ባህል ቱሪዝምና ቅርስ ቢሮ የቱሪዝም ዳይሬክተር አቶ ሳሚ አብዱልዋሲ በበኩላቸው ኤምባሲው ያከናውነው ስራ በክልሉ የሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎች ተደራሽነታቸው እንዲሰፋ የሚያስችል ነው ብለዋል።