መተማ፤ መጋቢት 7/2017(ኢዜአ)፡- በምዕራብ ጎንደር ዞን ባለፉት ስምንት ወራት ከስምንት ሺህ ለሚበልጡ ሰዎች የሥራ እድል መመቻቸቱን የዞኑ ሥራ እና ሥልጠና መምሪያ አስታወቀ።
አስተያየታቸውን የሰጡ የሥራ እድል የተፈጠራለቸው ሰዎች፤ ተደራጅተው በተሰማሩባቸው ዘርፎች ገቢ በማግኘት ተጠቃሚ መሆን እንደጀመሩ ተናግረዋል።
የመምሪያው ምክትል ኃላፊ አቶ አስፋው በሪሁን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአካባቢውን ፀጋ በመለየት ወጣቶችን የሥራ እድል ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ነው።
ባለፉት ስምንት ወራት ከስምንት ሺህ ለሚበልጡ ሰዎች በተለያዩ ዘርፎች የሥራ እድል እንደተመቻቸላቸው አስታወቀዋል።
የሥራ እድሉ የተመቻቸላቸው በእንስሳት እርባታ፣ በመስኖ፣ በኮንስትራክሽን፣ በቤትና ቢሮ እቃዎች ማምረት፣ በማዕድንና በሌሎች የአገልግሎት ዘርፎች መሆኑን ጠቅሰዋል።
ከአምስት ሺህ ካሬ ሜትር በላይ የመሥሪያና መሸጫ ቦታ እንደተሰጣቸውም ገልጸዋል።
የሥራ እድል ከተመቻቸላቸው መካከል የገንዳ ውሃ ነዋሪ ወይዘሮ አለም ውበት በሰጡት አስተያየት፤ ከሌሎች ጓደኞቻቸው ጋር ተደራጅተው በዶሮ እርባታ ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል።
በተሰጠን ሼድ የአንድ ቀን ጫጩት በማስመጣት አሳድገን ስንሸጥ ቆይተናል፤ አሁኑ ደግሞ እንቁላል ጣይ ዶሮዎችን በመጨመራችን ከእንቁላል ሽያጭ ተጨማሪ ገቢ እያገኘን ነው ብለዋል።
ሌላኛው በዚሁ ከተማ በቤትና ቢሮ እቃዎች ስራ የተሰማራው ወጣት ሷልህ አብዱ በበኩሉ፤ ከስድስት ጓደኞቹ ጋር ተደራጅተው በተመቻቸላቸው የሥራ እድል በመሰማራት ገቢ እያገኙ ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን ገልጿል።
መንግስት የመሥሪያና መሸጫ ቦታ እንደሰጣቸው ጠቅሶ፤ ሥራቸውን በስፋት ለመቀጠል የብድር አቅርቦት እንደሚፈልጉ አመልክቷል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን ባለፈው በጀት ዓመት 26ሺህ ለሚሆኑ ሰዎች የሥራ እድል መፈጠሩን ከዞኑ ሥራ እና ሥልጠና መምሪያ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።