ሰመራ፤ መጋቢት 19/2017(ኢዜአ)፡- የኢንፎርሜሸን ቴክኖሎጂ መሠረታዊ ዕውቀት ማስጨበጥ የሚያስችል ተንቀሳቃሽ የአይ ቲ ቤተ ሙከራ ስልጠና በሠመራ ከተማ ለሚገኙ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎችና መምህራን በመሰጠት ላይ ይገኛል።
በስልጠናው ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የአፋር ክልል ትምህርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሁመድ አብደላ እንዳሉት ስልጠናው ለሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች መሰረታዊ የኢንፎርሜሸን ቴክኖሎጂ ዕውቀትን በማስጨበጥ በዲጂታል ዓለም ላይ ግንዛቤ እንዲኖራቸው የሚያደርግ ነው።
ይህም በዲጂታል ቴክኖሎጂ ለምናደርገው ጉዞ ተማሪዎቹ በአቅራቢያቸው መለማመድ የሚያስችላቸው ነው ብለዋል
በቀጣዮቹ ቀናትም ተማሪዎች ይህን ዕድል በመጠቀም ስልጠናውን በመውሰድ ተጠቃሚ መሆን እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል።
በ አይ ኮ ግ(I cog) ኮንሰልታንት የዲጂትራክ(digtruck) ፕሮጀክት ኃላፊ ወይዘሪት ኤሌኒ ክፍሌ በበኩላቸው እንዳሉት የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች መሠረታዊ የሆነ የአይ ቲ እውቀት እንዲኖራቸው ዓላማ ያደረገ ስልጠና መሆኑን ተናግረዋል።
ሰልጣኞች ባሉበት ሆነው በተንቀሳቃሽ ቤተ ሙከራ ውስጥ መሠረታዊ የኮምፒዩተርና የኢንተርኔት ትውውቅ እንደሚኖራቸው ገልጸው የሮቦትና የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስን ምንነት ለማወቅ ይችላሉ ብለዋል።
ከሰመራ ከተማ አልፎም በተመረጡ 10 የክልል ከተሞች ከ3ሺህ 500 በላይ ተማሪዎች የስልጠናው ተጠቃሚ እንደሚሆኑ የገለፁት ኃላፊዋ ከሠመራ ከተማም 400 ተማሪዎች እንደሚወሰዱ ተናግረዋል።
ከስልጠናው በኋላም ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመነጋገር በትምህርት ቤቶች የኮዲንግ ክበብ ሊቋቋም እንደሚችልም ጠቁመዋል።
ስልጠናው ተማሪዎቹን ለኢትዮጵያ ኮደርስ ስልጠና መሠረት እንደሚሆናቸውና ጥረታቸውን አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
ስልጠናው ለተከታታይ ሃያ ቀናት እንደሚሰጥም ተመላክቷል።