የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

ኮሌጁ ተወዳዳሪ የሰው ኃይልን በማፍራት የአካባቢውን እንዱስትሪና ኢንቨስትመንት እየደገፈ ነው

Apr 14, 2025

IDOPRESS

ደብረብርሀን፤ ሚያዚያ 4 / 2017(ኢዜአ) ፡-የደብረ ብርሃን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ብቁና ተወዳዳሪ የሰው ኃይልን በማፍራት በአካባቢው እያደገ የመጣውን ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ለመደገፍ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ አስታወቀ።

ኮሌጁ "ብሩህ አዕምሮዎች በክህሎት የበቁ ዜጎች" በሚል መሪ ሃሳብ የክህሎት፣ የቴክኖሎጂና የጥናትና ምርምር ስራዎች ውድድር አካሄዷል።

የደብረ ብርሃን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዋና ዲን አቶ ባሻዬ በየነ እንደገለጹት የአገራችን ኢኮኖሚ የሚፈልገውን በመካከለኛ ደረጃ የሰለጠነ የሰው ሃይል ማምረት ከቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች የሚጠበቅ ነው።

በአሰልጣኞች፣ በሰልጣኞችና በኢንተርፕራይዞች ደረጃ የተካሄደው ቴክኖሎጂን የመቅዳት፣ የማላማድና የማሸጋገር ውድድር በቀጣይ ኢኮኖሚውን ለመደገፍ ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል።

ይህም ለአገራችን ኢኮኖሚ ውጤታማ የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን ይዘው የሚቀርቡ ተወዳዳሪዎችን በመለየትና እውቅና በመስጠት በቀጣይ ለህብረተሰብ ጥቅም እንዲውሉ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል።

በተጨማሪም አሰልጣኞች፣ ሰልጣኞችና ኢንተርፕራይዞች እርስ በእርስ በመተዋወቅ፣ ተሞክሮ በመለዋወጥና በቅንጅት በመስራት ወደ ላቀ ደረጃ እንዲሸጋገሩ እድልን የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል።


የደብረ ብርሃን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የማኑፋክቸሪንግ ትምህርት ክፍል መምህር የሆኑት ህይወት አስናቀ እንደገለጹት ኤሌክትሪካል የወተት መናጫ ማሽን በመስራት ለውድድሩ መቅረባቸውን ተናግረዋል።

ያቀረቡት ቴክኖሎጂም በ20 ደቂቃ ውስጥ ወተቱን በመናጥ ጥራት ያለው ቅቤ ለማምረት የሚያስችል ነው።

የዌብ ዴቨሎፕመንትና ዳታ ቤዝ አድሚኒስትሬሽን ሰልጣኝ የሆነው ባየሁ ገበየሁ በበኩሉ ባለብዙ ልኬት የአፈር መመርመሪያና መረጃ ማከማቸት የሚችል ቴክኖሎጂ ይዞ በመቅረቡ ለአሸናፊነት መብቃቱን ተናግሯል።

ቴክኖሎጂው የአፈሩን የማዕድን ዓይነት፣ ሙቀት፣ ርጥበትና አሲዳማነት በመለየትና መሬቱን በማከም ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል መሆኑን አስረድቷል።

ከኢንተርፕራይዞች መካከልም አቶ ኢያሱ ገረመው እንደገለጸው ስንዴ፣ ገብስ፣ ባቄላ፣ ሸንብራና ጤፍን በቀን እስከ 200 ኩንታል መውቃት የሚችል ማሽን ለውድድር ይዞ መቅረቡን አስረድቷል።


ከውጭ እስከ 1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ብር ወጪ ይገባ የነበረውን የእህል መውቂያ ማሽን ከ400 ሺህ ብር ባልበለጠ ዋጋ ለአርሶ አደሩ የሚቀርብ በመሆኑ አዋጭ ነው ብለዋል።

በደብረ ብርሃን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በተዘጋጀው የቴክኖሎጂ ውድድር ላይም በዞኑ የሚገኙ የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች በተወዳዳሪነት መሳተፋቸውም ተመላክቷል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.