አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2017(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የበዓል ገበያ አስፈላጊ ምርቶች በበቂ መጠን መቅረባቸውን ሸማቾችና ነጋዴዎች ገለፁ።
በነገው እለት የትንሳኤ በዓል የሚከበር ሲሆን ኢዜአ የበዓሉ ግብይት ድባብ ምን ይመስላል የሚለውን ተዘዋውሮ ቃኝቷል።
ተዘዋውረን ባየናቸው የሸጎሌ የእንስሳት እንዲሁም የፒያሳ የእሁድ ገበያዎች ለበዓል አስፈላጊ የሆኑ ምርቶች ቀርበዋል።
በሸጎሌ የከብት ገበያ ያነጋገርናቸው አንዳርጌ ታደሰ እንዳሉት፤ ለበዓሉ በቂ የሆነ የእንስሳት አቅርቦት አለ።
ሌላው አስተያየት ሰጪ ንቁ ፈርጃ በበኩላቸው፤ በገበያው በቂ የእንስሳት አቅርቦት መኖሩን ገልጸዋል።
ሲገበያዩ ያገኘናቸው አቶ ብርሃኑ ጮንቄም እንዲሁ በአቅም ልክ ግብይት መፈፀም የሚቻልበት ገበያ መኖሩን ተናግረዋል።
በገበያው የእርድ እንስሳት ሲሸጡ ያገኘናቸው ዚያድ አሊይ በበኩላቸው፤ ለበዓሉ በቂ የእርድ እንስሳት ይዘው መቅረባቸውንና ሸማቾች እየተገበያዩ መሆናቸውን ገልፀዋል።
ሲገበያዩ ያገኘናቸው አቶ ሁሴን ሳኒዮአሊ በበኩላቸው፤ ለበዓሉ በቂ አቅርቦት በመኖሩ ሸማቹ በአቅሙ እየተገበያየ ይገኛል ብለዋል።
በፒያሳ የእሁድ ገበያ ሲገበያዩ ያገኘናቸው ሸማቾች በበኩላቸው፤ በእሁድ ገበያ ምርቶችን በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት መቻላቸውን አስረድተዋል።
ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል የዓይኔአበባ ጌታቸው በእሁድ ገበያ የህብረተሰቡን አቅም ባማከለ መልኩ ምርቶች መቅረባቸውን ተናግረዋል።
ሌላው አስተያየት ሰጪ ሲዳ ከበደ እንደገለጹት፤ አቅምን ያገናዘበ አቅርቦት መኖሩን ገልጸዋል።
በእሁድ ገበያ ምርታቸውን ይዘው ከቀረቡት ነጋዴዎች መካከል እምሻው ብርቄና ሄለን ብስራት በተመጣጣኝ ዋጋ ምርቶችን ይዘው መቅረባቸውን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያውያን ወትሮም ቢሆን መረዳዳት ባህላችን ነውና በዓሉን ያለው ለሌለው በመስጠት ሊያሳልፍ እንደሚገባም ነው አስተያየት ሰጪዎቹ የገለጹት።