አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 13/2017(ኢዜአ)፦ በማምረቻው እና በወጪ ንግድ ላይ የተሰማሩ ባለሃብቶች መንግስት የፈጠረው ምቹ ሁኔታ ውጤታማ እንዳደረጋቸው ገልጸዋል፡፡
በርካታ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ የተፈጠረውን ምቹ የንግድ ከባቢ ሁኔታ በመጠቀም መዋዕለ ንዋያቸውን በስፋት በማፍሰስ እየሰሩ ይገኛሉ፡፡
በተለይም መንግስት የአምራች ዘርፉን ለማበረታታት የዘረጋቸው አዳዲስ የአሰራር ማዕቀፎች በርካቶቹን ተጠቃሚ ማድረግ ጀምሯል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ያነጋገራቸው ባለሃብቶች መንግስት በልዩ ትኩረት የግሉን ዘርፍ ከማበረታታት ጀምሮ በርካታ ድጋፎችን ማድረጉ ውጤታማ እያደረጋቸው እንደሚገኝ አስታውቀዋል፡፡
ሳቢያ የውሃ ቆጣሪ አምራች ድርጅት ስራ አስኪያጅ አይንሸት አስረስ(ዶ/ር) ከዛሬ ስድስት አመት በፊት የውሃ ቆጣሪ የሚያመርት ድርጅት ማቋቋማቸውን ተናግረዋል፡፡
በቀጣይ ከሀገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ምርታቸውን ወደ ተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ለመላክ ዝግጅት ማጠናቀቃቸውን አስታውቀዋል፡፡
ለድርጅቱ ስኬት የመንግስት ክትትልና ድጋፍ ወሳኝ እንደነበር ያነሱት ስራ አስኪያጁ መንግስት ከማበረታታት በተጨማሪ በርካታ ድጋፍ እያደረገላቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በኢንዱስትሪ መንደር የማምረቻ ቦታ እንደተሰጣቸው ተናግረው በቀጣይ ምርታቸውን በማሳደግ ይበልጥ ውጤታማ ለመሆን በትኩረት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል፡።
የማክሮ ፋርም ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ፋሲል ታረቀኝ በበኩላቸው የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ የተለያዩ የሰብልና የጥራጥሬ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ ውጤታማ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል፡፡
መንግስት የውጭ ምንዛሬ እንድናገኝ ምቹ ሁኔታ ፈጥሮልናል ያሉት አቶ ፋሲል አሁን ላይ ምርቶችን ከገበሬዎች፣ ከምርት ገበያ እና ከህብረት ስራ ማህበራት በቀላሉ ለማግኘት ችለናል ሲሉ ገልጸዋል፡፡
በተጨማሪም ከገበሬዎች ጋር በመተባበር ለውጭ ገበያ የሚቀርብ ምርት እንድናመርት ትልቅ እገዛ ተደርጎልናል ነው ያሉት፡።
መንግስት ምርቶቻቸውን በቀላሉ ወደተለያዩ መዳረሻ ሀገራት እንዲልኩ የሚያደርግላቸው ድጋፍ ውጤታማ እንዳደረጋቸው አንስተዋል፡፡
በመንግስት እየተደረገ ያለው ድጋፍ በዘርፉ የተሰማሩ ባለሀብቶችን ተጠቃሚ እና ውጤታማ እያደረጋቸው እንደሆነም ስራ አስኪያጁ ጨምረው ተናግረዋል፡፡
ድርጅታቸው በጥራጥሬና ቅባት እህል ዘርፍ የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በቀጣይም የበለጠ ውጤታማ ለመሆን እንደሚሰሩ አስታውቀዋል፡፡