አዲስ አበባ፤ግንቦት 8/2017(ኢዜአ)፦ባለፉት ዓመታት ዲጅታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በተከናወኑ ስራዎች ጉልህ ስኬቶች መመዝገባቸውን የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ ገለፁ።
ፕሬዚዳንት ታዬ፣በምስራቅ አፍሪካ የመጀመሪያ የሆነውን የቴክኖሎጂ ኤክስፖ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሸን ማዕከል በይፋ ከፍተዋል።
በመክፈቻ ንግግራቸውም፥ ባለፉት ዓመታት ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተለያዩ መሰረተ ልማቶች መገንባታቸውን ጠቅሰውጸ ይህም ለዘርፉ የተሰጠውን ትኩረት ያሳያል ብለዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን ቀርጾ በመተግበርም የዲጂታል ምህዳርን እና የወጣቶችን የፈጠራ ባህልን ማጎልበት መቻሉን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ በዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ለአፍሪካ ምሳሌ የሚሆን አቅም ለመገንባት ትኩረት ሰጥታ እየሰራች ነው ብለዋል።
ተለዋዋጩን ዓለምአቀፍ ሁኔታ ታሳቢ ያደረገ የቴክኖሎጂ አቅም መገንባት ሁለንተናዊ ደህንነትንና የተሟላ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑንም ገልፀዋል።
ኢትዮጵያ ዲጂታል የክፍያ ስርዓት ተግባራዊ ማድረጓ የፋይናንስ ስርዓቱን ቀልጣፋና ተደራሽ እንዲሆን ማድረጉንም አንስተዋል።
ኤክስፖው በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ያተረፉ በርካታ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ይሳተፉበታል።