አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2017(ኢዜአ)፦ ግብርናን በተሻለ መንገድ የሚመሩ የጥናትና ምርምር፣ አዳዲስና በቴክኖሎጂ የታገዙ አሰራሮችን የሚያሳልጡ ተቋማት ግንባታ በዘርፉ ከፍ ያለ እመርታ የሚያመጡ ናቸው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሁለተኛው የብራዚል-አፍሪካ የምግብ ዋስትና፣ ረሃብን መዋጋት እና የገጠር ልማት ጉባኤ በብራዚሏ ዋና ከተማ ብራዚሊያ መካሄድ መጀመሩን ገልጸዋል።
መድረኩ የግብርና ምርትን እድገት፣ የገጠር ልማትንና የምግብ ዋስትናን ማሻሻል ላይ ትኩረት ያደረገ መሆኑንም አስታውቀዋል።
ግብርናን በተሻለ መንገድ የሚመሩ የጥናትና ምርምር፣ አዳዲስና በቴክኖሎጂ የታገዙ አሰራሮችን የሚያሳልጡ ተቋማት ግንባታ በዘርፉ ከፍ ያለ እመርታ የሚያመጡ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ በፖሊሲ የተደገፈ መሰረታዊ የለውጥ ስራዎችን በመተግበር የግብርናውን ዘርፍ ከፍ ባለ እመርታ ላይ ለማስገኘት የሰራችውንና እየሰራች ያለውን ተሞክሮ በጉባዔው ታቀርባለች የሌሎችንም ትጋራለች ብለዋል።
በመድረኩ የእውቀት ሽግግር እና የደቡብ-ደቡብ ትብብርን በመጠቀም የምግብ ስርዓታችንን ሊያጠናክሩ የሚችሉ የመስክ ምልከታዎችን፣ የልምድ ልውውጦችንና ስምምነቶችን እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል።