አዲስ አበባ፤ ሰኔ 13/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ለዘላቂና ሁሉን አቀፍ የልማት ስራዎች የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት(ተመድ) አስታወቀ።
ተመድ በኢትዮጵያ የተለያዩ ዘላቂ የልማት ስራዎችን መደገፍ የሚያስችል የስድስት ነጥብ አምስት ቢሊዮን ዶላር የድጋፍ ስምምነት አድርጓል።
ስምምነቱን የተመድ ረዳት ዋና ጸሀፊ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ ዶክተር ራሚዝ አላካባሮቭ እና የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው ፈርመውታል።
ስምምነቱ ኢትዮጵያ ቀጣይነት ያለውና ሁሉን አቀፍ ልማት ለማረጋገጥ የምታደርገውን ጥረት የመደገፍ ዓላማ እንዳለው ተገልጿል።
ለአምስት አመት በሚተገበረው ስምምነት በኢትዮጵያ ኢኮኖሚን ለማሳደግ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ ለኢነርጂ ልማት፣ ለትምህርት፣ ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከል እና ለሌሎች ዘርፎች እንደሚውልም ተመላክቷል።
የተመድ ረዳት ዋና ጸሀፊ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ ዶክተር ራሚዝ አላካባሮቭ በወቅቱ እንደገለጹት ድጋፉ የኢትዮጵያ የልማት ስራዎችን ለማገዝ ያስችላል።
በቀጣይም ተመድ በኢትዮጵያ ለሚከናወኑ የልማት ስራዎች የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው በበኩላቸው፤ የትብብር ስምምነቱ ኢትዮጵያ ለምታከናውናቸው የልማት ስራዎች ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት እያደረገ ላለው ድጋፍ ምስጋና አቅርበው፤ ለስምምነቱ ውጤታማነት በትኩረት ይሰራል ብለዋል።