ሆሳዕና ፤ ሰኔ 18/2017(ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በግብርናው ዘርፍ እየተመዘገቡ ያሉ ተስፋ ሰጪ ስኬቶችን የማስቀጠሉ ተግባር በተቀናጀ መንገድ እንደሚጠናከር የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶር) ገለጹ፡፡
"የግብርና ሴክተር ምሶሶዎችን በማሳካት የበለፀገ ቤተሰብ ለማየት እተጋለሁ" በሚል መሪ ሀሳብ በግብርና ትራንስፎርሜሽን አቅጣጫዎች ዙሪያ ለግብርና ልማት ሰራተኞች የተዘጋጀ ስልጠና በሆሳዕና ከተማ ተሰጥቷል፡፡
የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው (ዶር) በወቅቱ እንደተናገሩት፤ የሀገር ኢኮኖሚን ለማሳደግ ትኩረት ከተሰጣቸው አምስት ዘርፎች መካከል አንደኛው ግብርና ነው፡፡
ግብርናን ለማዘመን የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ ምርትና ምርታማነትን መጨመር ላይ ትኩረት ተሰጥቶታል ብለዋል፡፡
የግብርናው ዘርፍ ሁሉን አቀፍ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ስለመሆኑ ጠቁመዋል፡፡
በክልሉ ቀደም ሲል በተከናወኑ የግብርና ልማት ስራዎች ተስፋ ሰጪ ስኬቶች እየተመዘገቡ መሆናቸውን አንስተው፤የበለጠ ለማጠናከር በተቀናጀ መንገድ እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡
ለዚህም ክልሉ ያለውን መሬት በወቅት ሳይገደብ በአግባቡ በማልማት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የግብርና ልማት ባለሙያው ሚና ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡስማን ስሩር በበኩላቸው፤ የግብርና ዘርፍ ከድህነት የመውጫ መንገዳችን ነው ብለዋል፡፡
በክልሉ በግብርናው ዘርፍ የተመዘገቡ ስኬቶች እንዲጠናከሩ በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡
በስልጠናው ከሀድያ ዞን የተውጣጡ የግብርና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል፡፡