ክልል፤ ሰኔ 18/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የተከናወኑ እና በሂደት ላይ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች ለኢትዮጵያ እድገትና ብልፅግና ስኬት ብሩህ ተስፋ የሰነቁ መሆናቸውን የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ተናገሩ።
ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ተውጣጥተው ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጋር ውይይት ያደረጉ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች በአማራ ክልል ጎንደርና አካባቢው በመገኘት የልማት ስራዎችን ተመልክተዋል።
የጎርጎራ፣ መገጭ የመስኖ ፕሮጀክት፣ የጎንደር ከተማ ኮሪደርና የአፄ ፋሲል አብያተ መንግስታትና ሌሎችም ከተመለከቷቸው መካከል ይጠቀሳሉ።
የጉብኝቱ ተሳታፊዎች በክልሉ የተከናወኑ እና በስራ ላይ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች ከሀገራዊ ፋይዳቸው አንፃር እጅግ ጠቃሚና አስፈላጊ ናቸው ብለዋል።
በክልሉ የተከናወኑና በሂደት ላይ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች ለኢትዮጵያ እድገትና ብልፅግና ስኬት ብሩህ ተስፋ የሰነቁ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ለእነዚህ ዋና ዋና የልማት ስራዎች መሳካት ሁለንተናዊ እገዛና ክትትል በማድረግ እንዲሁም አቅጣጫ በመስጠት የላቀ ሚናቸውን ለተወጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ክብርና ምስጋና ይገባል ብለዋል።
ከምስራቅ ጉራጌ ዞን በግል ዲጂታል ሚዲያ ላይ የሚሰራው ኢብራሂም ምስጋናው፣ ከድሬዳዋ መገናኛ ብዙሃን ዘይነብ አህመድ እና ከምዕራብ ሐረርጌ የኮሙኒኬሽን ባለሙያው መሀመድ ኡስማን ፤ በክልሉ በሩቅ ሆነን በሶሻል ሚዲያ የምንሰማውና መጥተን ያየነው የተለያየ ነው ብለዋል።
በክልሉ ሌት ከቀን ለውጥና አስደናቂ የልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን በተግባር አረጋግጠናል ያሉት አስተያየት ሰጪዎቹ፤ ሰላም የሌለ በማስመሰል የሚናፈሱ ወሬዎች ሀሰት ስለመሆናቸው አንስተዋል።
ከሌሎች አስተያየት ሰጪዎች መካከል መልካሙ አብደታ ከኢዜአ እና ደምሰው መኩሪያ ከኢቲሺ በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢንሸቲቭ በክልሉ የተከናወኑ የልማት ፕሮጀክቶችን አድንቀዋል።
በአስደናቂ ጥበብ በሚያምር ሁኔታ የተገነባው የጎርጎራ ሪዞርት የእይታ ልህቀትና የህልም ስኬት ውጤት የታየበት የሀገር ሃብት መሆኑንም አንስተዋል።
የጎንደር ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ደብሬ የኋላ ፤ በጎንደር የሰሊጥ፣ የጥጥ እና ሌሎችም የግብርና ልማት ስራዎች የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥና ጎንደርን የሀገር ማዕድ የማድረግ ጥረት መሆኑን ገልጸዋል።
በቱሪዝም ዘርፍም አስደናቂ የመስህብ ስፍራና የሀገር ሀብት ያለበት መሆኑን ጠቅሰው ፤ በድምሩ ለጎንደር ሁለንተናዊ የልማት ስኬት የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ልዩ ትኩረት ፣ ድጋፍና ክትትል ትልቁን ድርሻ ይይዛል ብለዋል።
የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ከበደ ዴሲሳ፣ የጎንደርና አካባቢው ጉብኝት የልማት ጥረት ውጤት የታየበትና የሰላም እሴት ግንባታ እየተጠናከረ የመጣ መሆኑን ያየንበት ነው ሲሉ ገልጸዋል።
በድምሩ በተለያዩ አካባቢዎች የተከናወኑና በመከናወን ላይ ያሉ የልማት ስራዎች ኢትዮጵያ በከፍተኛ ደረጃ እየተገነባች መሆኑንና ብልፅግናዋ እውን እንደሚሆን የሚያረጋግጡ ማሳያዎች ናቸው ብለዋል።
በመሆኑም የወል ትርክትን በማፅናትና ኢትዮጵያዊ ሕብረ ብሄራዊ አንድነትን በማጠናከር የጋራ ልማትና እድገትን እውን ለማድረግ እንትጋ በማለት መልዕክት አስተላልፈዋል።