አዲስ አበባ፤ ሰኔ 26/2017(ኢዜአ)፦በምዕራብ ጉጂ ዞን በበልግ እርሻ በዘር ከተሸፈነው 368 ሺህ ሄክታር መሬት 8 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚጠበቅ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ።
በኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ የተመራ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች ቡድን በምዕራብ ጉጂ ዞን እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎችን እየጎበኘ ነው።
በዚህም በምዕራብ ጉጂ ዞን ሱሮ በርጉዳ ወረዳ በክላስተር የለማ ስንዴ እና ጤፍ ጎብኝቷል።
የምዕራብ ጉጂ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ ቱኬ አና ለከፍተኛ የስራ ሀላፊዎቹ በሰጡት ማብራሪያ፤ በዞኑ በተያዘው የክረምት ወራት 368ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ የዘር ዓይነት መሸፈኑን ገልጸዋል።
እነኚህም በቆሎ፣ ስንዴ፣ ቦሎቄ፣ ጤፍ፣ ማሾ እና ሌሎችም መሆኑን ጠቁመው፤ ከዚህም 8 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚጠበቅ ተናግረዋል።
የአርሶ አደሩ የሥራ ባህል ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሆኑንም አንስተዋል።
ምርታማነት እንዲያድግም መንግስት የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገ መሆኑን ጠቁመው ምርጥ ዘር፣ ማዳበሪያ እና ሌሎች ግብዓቶችን ማቅረቡንም ተናግረዋል።
በምዕራብ ጉጂ ዞን እየተካሄደ በሚገኘው የልማት ስራዎች ጉብኝት የክልሉ ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳን ጨምሮ በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ከፍያለው ተፈራ እንዲሁም ሌሎች የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ።