የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

<p>በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች የሰነዶች ማረጋገጥና ምዝገባ አገልግሎትን ለማዘመን እየተሰራ ነው- አገልግሎቱ</p>

Feb 12, 2025

IDOPRESS

ሀዋሳ፤ የካቲት 4/2017(ኢዜአ)፦ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች የሰነዶች ማረጋገጥና ምዝገባ አገልግሎትን ለማዘመን እየተሰራ መሆኑን የፌዴራል የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት አስታወቀ።

የፌዴራል የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት በመረጃ መረብ የተደገፈ የሰነዶች ማረጋገጥና ምዝገባ አገልግሎትን በሀዋሳ ከተማ ዛሬ በይፋ አስጀምሯል።

የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀሚድ ኪኒሶ በሥነ ስርዓቱ ላይ እንዳሉት፣ የሰነዶች ማረጋገጥና ምዝገባ አገልግሎትን ለማዘመን፣ ለማቀላጠፍና ተዓማኒነት ያለው ለማድረግ እየተሰራ ነው።


በአዲስ አበባ ከተማ በ16 እንዲሁም በድሬዳዋ ከተማ በአንድ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት አገልግሎቱ በዘመናዊ መንገድ በበይነ መረብ የቀጥታ አገልግሎት ታግዞ እየተሰጠ መሆኑንም ተናግረዋል።

ይህን አገልግሎት ወደ ሌሎች ክልሎችም ለማስፋት ከክልሎች ጋር የጋራ መድረኮችን በማካሄድ የግንዛቤ ፈጠራ ሥራ መሰራቱን ጠቅሰዋል።

ከዚህ ቀደም በሐረሪ፣ በቤንሻንጉል ጉምዝና በአማራ ክልሎች ዘመናዊና በበይነ መረብ የታገዘ አገልግሎት ሲሰጥ መቆየቱን አስታውሰው፣ በዛሬው ዕለትም አገልግሎቱ በሲዳማ ክልል መጀመሩን ተናግረዋል።

በበይነ መረብ ታግዞ የሚሰጠው አገልግሎት የተገልጋይን እንግልት የሚያስቀርና ጊዜ ቆጣቢ መሆኑንም ገልጸዋል።

በሀገር አቀፍ ደረጃ ወጥ የሆነ የሰነዶች ማረጋገጥና ምዝገባ አገልግሎት እንዲኖር ለማድረግ ድጋፍ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።


የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ መኩሪያ መርሻዬ በበኩላቸው፣ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት አሰጣጥ በበየነ መረብ ታግዞ መጀመሩ ዲጅታል ኢትዮጵያን ለመፍጠር የሚደረገው ጥረት አንዱ ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል።

ይህም ከዘመናዊ ቴክኖሎጂ ጋር የተቀራረበ ትውልድ ለመፍጠር ያግዛል ብለዋል።

ሀዋሳ ከተማን ስማርት ሲቲ ለማድረግ የተለያዩ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰው፣ በከተማዋ የፍትህ አገልግሎትን ከወረቀት ነጻ ለማድረግ በቴክኖሎጂ ታግዞ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።

ይህም የፍትህ አገልግሎት አሰጣጡን ከማጠናከር ባለፈ የተገልጋዩን ጊዜ በመቆጠብና እንግልቱን በማስቀረት በኩል ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን ነው የገለጹት።

ቀደም ሲል በፍርድ ቤቶች ይከሰት የነበረው የፋይል መጥፋትና ሌሎች ችግሮችን ማስቀረቱንም ጠቁመዋል።


የሲዳማ ክልል ፍትህ ቢሮ ሀላፊ አቶ ማቶ ማሩ የሰነዶች ምዝገባና ማረጋገጫ አገልግሎትን ማዘመኑ በፍትህ አሰጣጥ ሂደት የሚያጋጥሙ እንግልቶችን ለማስቀረት ያግዛል ብለዋል።

ፍርድ ቤቶች የተገልጋዮችን ሰነድ ትክክለኛነት ለማረጋገጥ የሚወስድባቸውን ጊዜ ለማሳጠርና ቀልጣፋና ፈጣን ፍትህ ለመስጠት እንደሚያስችልም አስረድተዋል።

አገልግሎቱን በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች ለማስፋት ቢሮው ከሰነዶች ምዝገባና ማረጋገጫ አገልግሎት ጋር በጋራ ይሰራል ሲሉም አረጋግጠዋል።

በሥነ ስርዓቱ ላይ አገልገሎቱን በክልሉ በንሳ ወረዳም ለማስጀመር የሚያስችል የስምምነት ሰነድ በክልሉ ፍትህ ቢሮ ሀላፊ በአቶ ማቶ ማሩና በአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀሚድ ኪኒሶ ተፈርሟል።

በመርሃ ግብሩ ላይ የፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት፣ የሲዳማ ክልል ፍትህ ቢሮና የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር አመራሮች ተገኝተዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.