የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
የአፍሪካ ህብረት

<p>በጂንካ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ከተማዋን ውብ፣ ፅዱና ለነዋሪዎቿ ምቹ አድርጓታል - የከተማዋ ነዋሪዎች</p>

Feb 14, 2025

IDOPRESS

ጂንካ፤ የካቲት 6/2017(ኢዜአ)፡- በጂንካ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ከተማዋን ውብ፣ ጽዱና ለነዋሪዎቿ ምቹ ማድረጉን አስተያየታቸውን የሰጡ የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ።

የኮሪደር ልማቱ ከተማዋን በቱሪስቶች ተመራጭ እንድትሆን እያደረጋት መሆኑንም ነዋሪዎቹ ተናግረዋል።


ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አቶ ሀብታሙ ወልዴ እንደገለጹት፤ የኮሪደር ልማቱ ጂንካ ከተማን ውብና ፅዱ በማድረግ ገጽታዋን እየቀየረ በመሆኑ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል።


የኮሪደር ልማት ለከተማዋ ፈጣን እድገት ፋይዳው የጎላ መሆኑን የገለጹት ደግሞ ሌላው የከተማዋ ነዋሪ አቶ ተስፋዬ ታደሰ ናቸው።

ከዚህ ቀደም የከተማዋ ዋና ዋና መንገዶች ጠባብ በመሆናቸው የትራፊክ አደጋ በተደጋጋሚ ይከሰት እንደነበር አስታውሰው፣ በኮሪደር ልማቱ ከመንገድ ግራና ቀኝ የተሰራው የእግረኞች መንገድ አደጋውን ይቀንሰዋል የሚል እምነት እንዳላቸው ገልጸዋል።


የኮሪደር ልማቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ የገለጹት ደግሞ አቶ ግርማ ተካልኝ እና ወጣት ምጥን ተፈራ የተባሉ አስተያየት ሰጪዎች ናቸው።

ልማቱ ለከተማዋ ነዋሪዎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸው፣ በልማቱ የከተማዋ ገጽታ እየተለወጠ መምጣቱን ተናግረዋል።


በጂንካ ከተማ በንግድ ስራ ላይ የተሰማራችው ወጣት ምጥን ተፈራ፣ በአካባቢዋ የኮሪደር ልማት ሥራ ከመከናወኑ በፊት ከመንገድ ላይ የሚነሳው አቧራ የደንበኞቿን ምቾት ይነሳ እንደነበር አስታውሳለች።

በዚህም የዕለት ገቢዋ ላይ ተጽዕኖ አሳድሮ እንደነበር ገልጻ፣ የኮሪደር ልማቱ ይህን ችግር እንደፈታላት ተናግራለች።


ከዚህ ቀደም የከተማዋ ወጣቶች የእረፍት ጊዜያቸውን የሚያሳልፉበት የመዝናኛ ስፍራ በበቂ ሁኔታ እንዳልነበር የተናገረው ወጣት አረቡ ሰኢድ በበኩሉ፣ ልማቱ አማራጭ የመዝናኛ ስፍራዎች መፍጠሩን ገልጿል።

በተጨማሪም የጋራ ስፖርት መስሪያ እና ውድድሮች የሚያካሂዱባቸው ምቹ ስፍራዎች እንዲኖረው ተደርጎ መከናወኑንም ተናግሯል።


የጂንካ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃ ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ ማርቆስ ኃይሌ በከተማው በመጀመሪያ ምዕራፍ የኮሪደር ልማት 5 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የልማት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።

ለልማቱ ከ35 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት መመደቡን ጠቅሰው፣ የልማት ሥራው የእግረኛ መተላለፊያ መንገዶች፣ የአደባባይ ልማት፣ ፋውንቴን እንዲሁም የመንገድ ዳርና የመንገድ አካፋይ የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች መካተታቸውን ገልጸዋል።

በቀጣይም ጂንካ ከተማን ለኮንፍረንስ ቱሪዝም ተመራጭ ለማድረግ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸው፣ ለልማቱ የከተማው ማህበረሰብ ያልተቆጠበ ተሳትፎ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.