ደሴ፤ የካቲት 11/2017(ኢዜአ)፡- ምርት በመደበቅ፣ ዋጋ በመጨመርና በሌሎችም ህገ ወጥ ንግድ ላይ የተሰማሩ አካላትን በመለየት እየተወሰደ ያለው እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የደሴ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ።
በደሴ ከተማ ህገ ወጥ ንግድ ሲያከናውኑ የተገኙ 82 የንግድ ድርጅቶች እንዲታሸጉ መደረጉን የከተማ አስተዳደሩ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ አስታውቋል።
በዘርፉ ጎላ ያለ ህገ ወጥ ተግባር ፈጽመዋል የተባሉ 13 ግለሰቦችም ጉዳያቸው በህግ እንዲጠየቁ ለማድረግ በሂደት ላይ መሆኑንም ተገልጿል፡፡
የደሴ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ሽመልስ ጌታቸው፤ ከተማ አስተዳደሩ ገበያውን ለማረጋጋት በትኩረት እየሰራ ባለበት ወቅት የኑሮ ውድነት እንዲከሰት የሚሰሩ ህገ ወጥ ነጋዴዎችን አንታገስም ብለዋል፡፡
በዚህም ምርት በመደበቅ፣ ዋጋ በመጨመርና በሌሎችም ህገ ወጥ ንግድ ላይ የተሰማሩትን በመለየት እየተወሰደ ያለው እርምጃ ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት፡፡
ህገወጦችን ሥርዓት ለማስያዝ እየተደረገ ያለውን እንቅስቃሴ በመደገፍ ህብረተሰቡ እያደረገ ያለው ትብበር ማጠናከር እንዳለበትም አመልክተዋል።
በቂ ምርት ከተለያየ አካባቢ ወደ ከተማው እየገባ መሆኑንም ምክትል ከንቲባው አረጋግጠዋል፡፡
የከተማ አስተዳደሩ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ዮናስ እንዳለ በበኩላቸው፤ በቅንጅት በተደረገ ክትትልና ቁጥጥር ያለ ምክንያት በምርት ላይ ዋጋ የጨመሩ፣ ምርት የደበቁ፣ ያለ ንግድ ፍቃድ ሲሰሩ የተገኙ 82 የንግድ ድርጅቶች ታሽገዋል ብለዋል፡፡
በተደረገ ክትትል እና ቁጥጥር በአምስት ሊትር ዘይት ላይ የ400 ብር እና በአንድ ኩንታል ስንዴ ዱቄት ላይ የ1ሺህ 600 ብር ጭማሪ የተደረገባቸው ምርቶችን መገኘታቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል።
ተከማችቶ የተገኘው ምርትም በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እንዲቀርብ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡
በዘርፉ ጎላ ያለ ህገ ወጥ ተግባር ፈጽመዋል የተባሉ 13 ግለሰቦችም ጉዳያቸው በህግ እንዲጠየቁ ለማድረግ በሂደት ላይ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በደሴ ከተማ አስተዳደር ለገበያ ማረጋጊያ ከተመደበው ገንዘብ በ20 ሚሊዮን ብሩ የተለያየ ምርት ተገዝቶ ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ መሆኑም ታውቋል፡፡
አዲስ አበባ፤ የካቲት 21/2017(ኢዜአ)፡- የምግብ ዋስትና እና ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ለነገ የሚተው የምርጫ ጉዳይ ባለመሆኑ በልዩ ትኩረት መረባረብ እንደሚገባ...
Feb 28, 2025
ሐረር፤ የካቲት 16/2017(ኢዜአ)፦ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ ሁሉን አቀፍ ስራዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት ያሳደጉ መሆናቸውን የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ ጥር 30/2017(ኢዜአ)፦የየካቲት ወር የነዳጅ ምርቶች የችርቻሮ መሸጫ ዋጋ በጥር ወር በነበረበት የሚቀጥል መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስ...
Feb 8, 2025