የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
የአፍሪካ ህብረት

<p>በክልሉ የሚሰበሰበውን ገቢ በአግባቡ በማስተዳደር ለልማት ስራዎች ማዋል ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ</p>

Feb 26, 2025

IDOPRESS

ባህርዳር፤ የካቲት 18/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የሚሰበሰበውን ገቢ በአግባቡ በማስተዳደር ለልማት ስራዎች ማዋል እንደሚገባ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ አስገነዘቡ።

"ግብር፣ ለሀገር ክብር" በሚል መሪ ሃሳብ የተዘጋጀ የዕውቅናና የታክስ ንቅናቄ መድረክ በባህር ዳር ከተማ ተካሂዷል።

ርዕሰ መስተዳድሩ በመድረኩ ላይ እንዳሉት፤ ክልሉ ካለበት ነባራዊ ሁኔታ አኳያ ገቢ የመሰብሰብ አቅምን በማሳደግ ሀብት መፍጠር ያስፈልጋል።


ለዚህም የገቢ አማራጮችን ለማስፋት ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ ሲሆን የሚሰበሰበውን ገቢም በአግባቡ ማስተዳደርና ለልማት ስራዎች ማዋል እንደሚገባ ገልፀዋል።

ገቢን በትልቁ መሰብሰብ ልማቱን ከማፋጠን በተጨማሪ የተረጋጋ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሁኔታ እንዲፈጠር አስቻይ መሳሪያ በመሆኑ ሁሉም አካል ኃላፊነቱን መወጣት እንዳለበት አስገንዝበዋል።

ባለፈው ዓመት ክልሉ በአስቸጋሪ የጸጥታ ችግር ውስጥ ሆኖም ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ለተወጡና ለዕውቅና ሽልማቱ ለበቁ የክልሉ ግብር ከፋዮች ምስጋና አቅርበዋል።


የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ ክብረት ሙሀመድ በበኩላቸው፤ ሀገራዊ የገቢ ሪፎርም የክልሉን ገቢ የመሰብሰብ አቅም በአራት እጥፍ ማሳደግ አስችሏል ብለዋል።

የክልሉን የጸጥታ ችግር እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ህገወጥ አሰራርን የተከተሉ ግለሰቦች መኖራቸውን ጠቅሰው በርካታ የክልሉ ግብር ከፋዮች ግን ኃላፊነታቸውን በአግባቡ በመወጣታቸው የተሻለ ገቢ እንዲሰበሰብ ማስቻሉን ገልፀዋል።


በክልሉ ባለፉት ሰባት ወራትም ከ31 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ እንደተቻለ ገልፀው፤ ይህን የተሻለ አሰራር በማጎልበት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።

የዚህ መድረክ ዓላማም የተጣለባቸውን ኃላፊነት በአግባቡ የተወጡትን ለማበረታታትና ዕውቅና ለመስጠት መሆኑንም አክለዋል።

በመድረኩ የክልሉና የፌዴራል አመራሮች እንዲሁም ምስጉን ግብር ከፋዮች ተሳትፈዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.