የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

<p>የኢትዮጵያን ምርቶች አዕምሯዊ ንብረት ጥበቃን ማጠናከር ይገባል</p>

Feb 27, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2017(ኢዜአ)፦ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ የኢትዮጵያን ምርቶች ዓለም አቀፋዊ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ የአዕምሯዊ ንብረት ጥበቃ ስራን ማጠናከር እንደሚገባ ተገለጸ።

ኢትዮጵያ በርካታ ምርቶችን ለውጭ ገበያ እያቀረበች ብትገኝም ከሌሎች ሀገራት ጋር ሲነፃፀር የሚገኘው ገቢ አነስተኛ መሆኑ ይነገራል።

በመሆኑም ይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን ምርቶቿ ዓለም አቀፍ እውቅና ኖሯቸው ተወዳዳሪነታቸው እንዲጨምር የአዕምሯዊ ንብረት ጥበቃ ሊደረግላቸው እንደሚገባ የዘርፉ ባለሙያዎች ገልጸዋል።

የህግ ባለሙያና የንግድ ምልክት ወኪል ሰላማዊት ዓለማየሁ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ በመልክዓ ምድራዊ አመላካች ሊጠበቁ የሚችሉ በርካታ ምርቶች ቢኖሩም በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ያገኙት ግን ጥቂቶች ናቸው።

"መልክዓ ምድራዊ አመላካች" የሚባለው የአንድ አካባቢ ምርት ባለው ልዩ ጥራት፣ ዝና፣ ተቀባይነትና ተመራጭነት ሲኖረው ነው ያሉት ባለሙያዋ፥ ምርቶቹ የአዕምሯዊ ጥበቃ ሲደረግላቸው የኢኮኖሚ ጠቀሜታቸው የጎላ ይሆናል ብለዋል።

የይርጋጨፌ፣ ሐረርና ሲዳማ ቡና በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ማግኘታቸው ያላቸው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ከፍተኛ እንዲሆን ማስቻሉን ተናግረዋል።

ሌሎች ምርቶችም በመልክዓ ምድራዊ አመላካች ምዝገባና ጥበቃ እንዲደረግላቸው በማድረግ በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና እንዲያገኙ በማድረግ የአካባቢውና የሀገርን ተጠቃሚነት ማሳደግ እንደሚገባ ተናግረዋል።

የአዕምሯዊ ንብረት ጥበቃ ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን ለምታከናውነው ተግባር አጋዥ መሆኑንም ጠቁመዋል።


የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር እንዳሉ ሞሲሳ ፥ ባለስልጣኑ አዕምሯዊ ንብረት ጠንካራ የህግ ጥበቃ እንዲያገኝ ጥናትና ምርምር በማድረግ ለመንግስት እያቀረበ ይገኛል ብለዋል።

ኢትዮጵያ በተለያዩ ምርቶች የታደለች ብትሆንም እነዚህን ምርቶች በቦታቸው፣ በጥራታቸውና በልዩ ባህሪያቸው የመልክዓ ምድራዊ አመላካች ጥበቃ እንዲያገኙ የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ እንዳልነበረ አውስተዋል።

አሁን ላይ የህግ ማዕቀፍ ዝግጅቱ እየተጠናቀቀ መሆኑን ጠቅሰዋል።

በሀገር ደረጃ የተመዘገቡ የቡና ምርቶችን በመልክዓ ምድራዊ አመላካች እንዲካተቱና ኢትዮጵያን ይበልጥ ተጠቃሚ እንዲያደርጉ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።

ሀገሪቱ ማግኘት የሚገባትን የውጭ ምንዛሬና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቷን ለማረጋገጥ ባለስልጣኑ የሚሰራውን ተግባር ሁሉም ሊደግፍ እንደሚገባም ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.