የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
የአፍሪካ ህብረት

<p>በትግራይ ክልል ህገ-ወጥ የወርቅ ማምረት ሥራ በሰዎችና እንስሳት ላይ ጉዳት እያስከተለ ነው</p>

Feb 27, 2025

IDOPRESS

ሽሬእንዳስላሴ፤ የካቲት 19/2017(ኢዜአ)፦ በትግራይ ክልል አደገኛ ኬሚካሎችን በመጠቀም የሚካሄድ ህገ-ወጥ የወርቅ ማምረት ሥራ በሰው፣ በእንስሳትና በተፈጥሮ ሃብት ላይ ጉዳት እያስከተለ መሆኑ ተገለጸ።

በክልሉ ሰሜናዊ ምዕራብ ዞን የደለል ወርቅ ክምችት ባለባቸው ወረዳዎች ከሚኖሩት መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው አርሶ አደሮች፤ በህገ ወጥ የወርቅ አምራቾች አካባቢው እየተጎዳና በሰዎች ላይም የጤና እክል እየደረሰ መሆኑን ገልጸዋል።

ከነዋሪ አርሶ አደሮቹ መካከል በዞኑ በሰየምቲ አዲያቦ ወረዳ የ''ምድረ ፈላሲ'' የገጠር ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር የዕብዮ ደብረፅዮን ምክንያቱ በውል በማያውቁት ምክንያት 15 ፍየሎቻቸው እንደሞቱባቸው ገልጸዋል።

የፍየሎቻቸው የሞት መንስኤ የሚጠጡት ውኃ ህገ-ወጥ የወርቅ አምራቾች በሚጠቀሙት ኬሚካል የተበከለ በመሆኑ መከሰቱን ቆይተው መገንዘባቸውን ተናግረዋል።

የዚሁ ገጠር ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ንጉሰ ምራጭ በበኩላቸው፣ ባልተለመደ ሁኔታ የጥጃዎች ሞቶ መወለድና የላሞች እርግዝና መጨናገፍ መበራከቱን አስረድተዋል።

በህገ-ወጥ የማዕድን አውጪዎች ምክንያት በዘፈቀደ የሚቆፈሩ ጉድጓዶች በግብርና ስራቸው ላይ እክል መፍጠሩን የገለፁት ደግሞ በዞኑ አስገደ ወረዳ የ''ሜሊ'' ገጠር ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አሰፋ የማነ ናቸው።

እንዲሁም ህገ-ወጥ የወርቅ አምራቾቹ በአካባቢያቸው የሚገኝ ወራጅ ወንዝ በባዕድ ነገር በመበከላቸው ያረቧቸው የነበሩ እንስሳት እንደሞቱባቸው ተናግረዋል።

በአክሱም ዩኒቨርሲቲ የሽሬ ካምፓስ አስተባባሪ ዳዊት ማሞ (ዶ/ር) በካምፓሱ የማዕድን ፋካሊቲ ምሁራን ባደረጉት ጥናት ለህገ-ወጥ ወርቅ የማውጣት ተግባር እየዋለ ያለው ኬሚካል በሰውና በእንስሳት ላይ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን አረጋግጠዋል ብለዋል።

በተለይ ሜርኩሪና ሲያናይድ የተባሉ አደገኛ ኬሚካሎችን ህገ-ወጥ በሆነ መንገድ በመጠቀም ወርቅ በሚመረቱባቸው አካባቢዎች የሚገኙ ወራጅ ወንዞችን መበከላቸውን አመልክተዋል።

ይህንን ተከትሎም በተለይ በእንስሳት ላይ የሞት አደጋ መከሰቱን በተደረገው ጥናት ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል።

እንዲሁም ህገ-ወጥ በሆነ የወርቅ ማምረት ስራ እዚህም እዛም ጉድጎዶችን በመቆፈር ለም አፈር እንዲሸረሸር እንዲሁም ደን እንዲወድም እያደረገ መሆኑንም በጥናቱ መረጋገጡን አስረድተዋል።

በዞኑ እየተስተዋለ ያለው ህገ-ወጥ የማዕድን ማውጣት ተግባር ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ እያመዘነ መሆኑን የገለፁት ደግሞ በአክሱም ዩኒቨርሲቲ የማእድን ፋካሊቲ ዲን አቶ በረከት ገብረስላሴ ናቸው።

እንደ እሳቸው ገለፃ የሚመለከተው አካል ህገ-ወጥ ድርጊቱን በተቀናጀ መልኩ ሊከላከል እንደሚገባም አፅንዖት በመስጠት አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.