የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
የአፍሪካ ህብረት

ሀገራዊ የትኩረት መስኮች የታለመላቸውን ውጤት እንዲያመጡ በምርምርና ጥናት መደገፍ ይገባል

Apr 3, 2025

IDOPRESS

ሆሳዕና፤ መጋቢት 19/2017(ኢዜአ)፡- ሀገራዊ የትኩረት መስኮች የታለመላቸውን ውጤት እንዲያመጡ በምርምርና ጥናት መደገፍ እንደሚገባ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የሚሰሩ ምሁራን አለመለከቱ።

"በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዘ የጥናትና ምርምር ስራን በማጠናከር የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንተጋለን" በሚል መሪ ሃሳብ በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የተካሄደው ሀገር አቀፍ የምርምር ኮንፍረንስ ተጠናቋል፡፡

በኮንፍረንሱ ማጠቃለያ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የኮንፍረንሱ ተሳታፊዎች እንዳሉት የጥናትና ምርምር ስራዎችን በቴክኖሎጂ ማስደገፍ ይገባል፡፡

በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ ፕሮፌሰር ይሰሀቅ ከቸሮ፤ ሀገራዊ የትኩረት መስኮች ተጨባጭ ውጤት እንዲያመጡ በምርምርና ጥናት ስራዎች መደገፍ አላባችው፡፡

በተለይም የጥናትና ምርምር ስራዎች ወደ ህብረተሰቡ ወርደው ለችግሮች መፍትሄ መስጠት እንዲችሉ በቴክኖሎጂ ማስደገፍ እንደሚገባም አመልክተዋል።

በርካታ ያደጉ ሀገራት ለምግብ ዋስትና መረጋገጥ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ተግባራዊ ማድረጋቸውን ያነሱት ፕሮፌሰሩ ሀገሪቱ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የምታደርገውን ጥረት ከግብ ለማድረስ የሚያግዙ የምርምር ስራዎች እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል።

ሌላኛው በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ ፕሮፌሰር ዲፒ ሸርማ በበኩላቸው፤ ከኢትዮጵያ የትኩረት መስክ መካከል የጤናና የትምህርት ዘርፎች ላይ የሚሰሩ ጥናቶች መብዛት አለባቸው ይላሉ።

በተለይም በእነዚህ መስኮች የሚሰሩ ስራዎችን ከሰው ሰራሽ አስተውሎት ጋር በማስተሳሰር የማህበረሰቡን ችግሮች በዘላቂነት መፍታት እንደሚገባም ጠቁመዋል።

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የህግ መምህርና ተመራማሪ ማንደፍሮ እሸቴ(ዶ/ር) እንደገለፁት የኢትዮጵያ ፈጣን ዕድገት እውን እንዲሆን በዲጂታል ቴክኖሎጂ ላይ የተጀመረው ጥረት መጠናከር አለበት፡፡

በምርምር ተቋማት የሚከናወኑ ስራዎች በሰው ሰራሽ አስተውሎት እንዲደገፉ ለማድረግ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የበኩላቸውን መወጣት እንዳለባቸው አመልክተዋል።

የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዳዊት ሀየሶ(ዶ/ር)፤ በዩኒቨርሲቲው የተዘጋጀው ሀገር አቀፍ የምርምር ኮንፍረንስ ችግር ፈቺ ጥናትና ምርምሮችን በሰው ሰራሽ አስተውሎት የተደገፉ እንዲሆኑ ልምድ የተወሰደበት ነው ብለዋል፡፡

በተጨማሪም ሀገሪቱ ለምትቀርጻቸው ፖሊሲዎች ግብዓት የሚሆኑ የምርምር ስራዎች የቀረቡበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በኮንፍረንሱ በሀገሪቱ ከሚገኙ የከፍተኛ ትምህርትና የምርምር ተቋማት የተውጣጡ ተመራማሪዎች ተሳትፈዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.