የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በመዲናዋ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 124 የተለያዩ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ ገብተዋል-ኮሚሽኑ

Apr 23, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 14/2017(ኢዜአ)፦በመዲናዋ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 124 የተለያዩ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ መግባታቸውን የአዲስ አበባ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ገለጸ።


የአዲስ አበባ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን የፕሮጀክቶች ክትትልና ድጋፍ ዳይሬክተር ብሩክ ተሆነ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ በመዲናዋ በርካታ ኢንቨስትመንትን የሚያበረታቱ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል።


በመዲናዋ ባለፉት ጥቂት አመታት የተገነቡ የኮሪደር፣ የቱሪዝም መሰረተ ልማቶችና መዳረሻዎች እንዲሁም ሌሎች የልማት ስራዎች ኢንቨስትመንቱ እንዲያድግ እያስቻሉ ነው ብለዋል።


በከተማዋ ምቹ ሁኔታ እየተፈጠረ በመሆኑም በተለይ በቱሪዝምና ሌሎች የአገልግሎት ዘርፎች ለመሰማራት በርካታ ባለሀብቶች ጥያቄ እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡


ኮሚሽኑ ይህን ታሳቢ በማድረግ የኢንቨስትመንት ፍቃድ በተቀላጠፈ ሁኔታ ከመስጠት በተጨማሪ ፍቃድ የወሰዱ ባለሀብቶች በፍጥነት ወደ ስራ እንዲገቡ ድጋፍና ክትትል እያደረገ መሆኑን አንስተዋል።


ባለፉት ዘጠኝ ወራት በኮንስትራክሽን፣ በትምህርት፣ በጤና፣ በአይሲቲ፣ በማኑፋክቸሪንግና በአገልግሎት ዘርፎች 124 ፕሮጀክቶች ወደ ስራ መግባታቸውን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።


ፕሮጀክቶቹ ከአስር ሺህ በላይ ለሆኑ ነዋሪዎች የስራ እድል መፍጠራቸውን ተናግረዋል፡፡


የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች በፍጥነት ወደ ተግባር መግባት ለከተማዋ ኢኮኖሚ ትልቅ ሚና እየተወጣ መሆኑንም አንስተዋል።


እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ፥ኮሚሽኑ አገልግሎቱን ለማዘመን ዲጂታላይዜሽን ላይ ውጤታማ ተግባራትን በማከናወን የኢንቨስትመንት ጉዳዮችን በቀላሉ በኦንላይን መፈጸም እንዲቻል አድርጓል፡፡


ከተማ አስተዳደሩ ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን በማንሳት፥ ባለሀብቶች በተለያዩ ዘርፎች ኢንቨስት እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.