የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በከተማው ከ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ የግብር ገቢ ተሰበሰበ

Apr 24, 2025

IDOPRESS

ጎንደር፤ሚያዚያ 15/2017 (ኢዜአ)፡-በጎንደር ከተማ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከተለያዩ የገቢ አርዕስቶች ከ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ የግብር ገቢ መሰብሰቡን የከተማ አስተዳደሩ ገቢዎች መምሪያ አስታወቀ፡፡


በከተማው 104 አዲስ ግብር ከፋዮችን ወደ ግብር መረቡ ማስገባት መቻሉንም መምሪያው ገልጿል፡፡


የመምሪያው ሃላፊ ወይዘሮ ጥሩዬ አትክልት ለኢዜአ እንደተናገሩት፥ በከተማው የገቢ አሰባሰብን በማዘመን ልማትን ለማፋጠን በተደረገው ጥረት በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ውጤታማ ስራ ማከናወን ተችሏል።


ይህም ከ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ በመሰብሰብ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፃር በ500 ሚሊዮን ብር ብልጫ እንዳለው አመላክተዋል፡፡


ከተለያዩ የገቢ አርዕስቶች በተሰበሰበው የግብር ገቢ የተሻለ ውጤት ማምጣት የተቻለው የንግድ ፣የኢንቨሰትመንትና የቱሪዝም ልማት ለማነቃቃት ምቹ ሁኔታ በመፈጠሩ እንደሆነ ገልጸዋል።


የግብር ስርዓቱን ዘመናዊና ቀልጣፋ ለማድረግ በ25 ሚሊዮን ብር እየተከናወነ ያለው የስማርት ቢሮዎችን የማደራጀትና የግብር ከፋዮችን መረጃዎች ወደ መረጃ ቋት የማስገባት ተግባር ሌላው መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡


በከተማው በደረጃ "ሀ" ከተመዘገቡ ከሁለት ሺህ በላይ ከፍተኛ ግብር ከፋዮች ደረሰኝ የመቁረጥና የተጠቃሚውን ደረሰኝ የመቀበል ባህሉን ለማሳደግ መሰራቱንም አክለዋል።


አዳዲስ ግብር ከፋዮችን ወደ ግብር መረቡ ለማስገባት በተደረገው እንቅስቃሴ 104 አዲስ ግብር ከፋዮችን ወደ ግብር መረቡ ማስገባት መቻሉን አስረድተዋል፡፡


በበጀት ዓመቱ ለመሰብሰብ የተቀመጠውን የገቢ ግብር እቅድ በቀሪ ወራቶች ለማሳካት ርብርብ እየተደረገ መሆኑንም ሃላፊዋ ተናግረዋል፡፡


የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ወይዘሮ ደብሬ የኋላ በበኩላቸው፤ ግብር መሰብሰብ ለከተሞች ልማትና እድገት መፋጠን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው የጎላ ነው ብለዋል።


የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት በሚደረገው ጥረት የንግዱ ማህበረሰብ ግብርን በመክፈል የዜግነት ግዴታውና ክብር መሆኑን በመረዳት ግብሩን በወቅቱ እንዲከፍል ጥሪ አቅርበዋል፡፡


ከከተማው ግብር ከፋዮች መካከል አቶ አወቀ ግስሙና አቶ ሰይድ ጀማው በሰጡት አስተያየት፤ በከተማው እየተከናወኑ የሚገኙት የልማት ፕሮጀክቶች ከፍተኛ በጀት የሚጠይቁ መሆናቸውን እንደሚረዱ ገልጸዋል።


በዚህም ግብራቸውን በወቅቱ በመክፈል የተጀመሩትን የልማት ስራዎች ለማጠናቀቅና አዳዲስ የሚጀመሩ ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን እየተወጡ መሆናቸውን ተናግረዋል።


የአስተዳደሩ ገቢዎች መምሪያ መረጃ እንደሚያሳየው ፤ በጎንደር ከተማ አስተዳደር ከ26ሺ በላይ ግብር ከፋዮች ይገኛሉ።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.