
ወላይታ ሶዶ፤ሚያዝያ 27/2017 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ለሀገር ብሄራዊ ጥቅም ሲባል የመንግስት ጠንካራ አቋምና ቁርጠኝነት የታየበት አዲስ የዲፕሎማሲ ምእራፍ መሆኑን ምሁራን ገለጹ።
በአፍሪካ የግዙፍ ኢኮኖሚና የበርካታ ህዝብ ባለቤት የሆነችው ኢትዮጵያ በቀጣናው የገበያ ዕድልና የእርስ በርስ ትስስር ለመፍጠር የሚያስችል እምቅ አቅምና ጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ አላት።
ኢትዮጵያ ከባህር በአጭር ርቀት ላይ የምትገኝ ሀገር ብትሆንም የቅርብ እሩቅ ተደርጋ መቆየቷ በብዙ መለኪያዎች ተጎጂ አድርጓታል።
በመሆኑም የለውጡ መንግስት እንዲህ አይነቱን የሀገር ማነቆ በመፍታት ለትውልዱ የተመቸችና የበለጸገች ሀገር ለመገንባት እየሰራ ይገኛል።
ለኢትዮጵያ የባህር በር ጉዳይ የህልውና ጉዳይ ነው ብሎ በመነሳት የመንግስት ሁለንተናዊ የዲፕሎማሲ ጥረት ተጠናክሮ ቀጥሏል።
በዚሁ ጉዳይ ኢዜአ ያነጋገራቸው በወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ የታሪክና ቅርስ አስተዳደር ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ አበሻ ሽርኮ (ዶ/ር)፤ መንግስት የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም በማስጠበቅ እየሄደበት ያለው የዲፕሎማሲ ጥረት የሚደነቅ መሆኑን ተናግረዋል።
በባህር በር ጉዳይ በመንግስት የተያዘው ጠንካራ አቋምና ቁርጠኝነት የሀገር ጥቅም ለማስጠበቅ የሚያስችል የዲፕሎማሲ ምዕራፍ የከፈተበት ታሪካዊ አጋጣሚ መሆኑንም አንስተዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ የቀጣናውን አገራት የምጣኔ ሃብት እድገት ለማጎልበትና ለአፍሪካ ነፃ የንግድ ትስስር ጥሩ መሰረት የሚያኖር መሆኑን ተናግረዋል።
በአፍሪካ ከናይጀሪያ በመቀጠል በህዝብ ብዛት ተጠቃሽ ለሆነችውና በምጣኔ ሃብቷ እያደገች ላለችው ኢትዮጵያ የባህር በር አማራጭ የሌለው የህልውና ጉዳይ ተደርጎ መያዙ ተገቢ መሆኑን አስረድተዋል።
በመሆኑም የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ የመንግስት ጥረት እንዳለ ሆኖ ሁላችንም በምንችለው አቅም የድርሻችንን መወጣት ይኖርብናል ብለዋል።
በርካታ የምዕራብና ምስራቅ ሀያላን ሀገራት በቀይ ባህርና ህንድ ውቂያኖስ ኮሪደሮች በሊዝና በኪራይ ፍላጎታቸውን እያራመዱ እየተጠቀሙ መሆኑን አንስተው ከቀይ ባህር በ60 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ያለችው የኢትዮጵያ መገፋት በየትኛውም መመዘኛ ተቀባይነት የሌለው መሆኑንም አንስተዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ከራሷም አልፎ ለቀጣናው አገራት የምጣኔ ሃብት ትስስርና አብሮ ለማደግ ወሳኝ በመሆኑ አገራት ሊተባበሩና የጋራ አጀንዳ ሊያደርጉ ይገባልም ብለዋል።

በዩኒቨርሲቲው የሚዲያና ኮሙኒኬሽን መምህርና ተመራማሪ ተሻለ ተገኑ (ዶ/ር) በበኩላቸው ቀይ ባህር የቀጣናው ሀገራት የትብብርና የቅንጅት ማዕከል በመሆን ለዘላቂ ሰላምና ዕድገት ወሳኝ ሚና አለው ብለዋል።
የትኛውም የበለጸገ ሀገር ከሌላው ጋር ሳይተባበር ያደገ የለም ያሉት ምሁሩ ዘመኑ የትብብር በመሆኑ በተለይም የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ከዚህ ልምድ ሊማሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ህግ እና የአፍሪካ ሀገራት በጋራ ለማደግና ለመልማት በተስማማችባቸው ሰነዶች መሠረት የባህር በርን በሰጥቶ መቀበል መርህ ተጠቃሚ እንድትሆን ያስችላታል ብለዋል።
የኢትዮጵያ መንግስት የትውልድ ጥያቄ የሆነውን የባህር በር ጉዳይ ለማሳካት ለሚያደርገው ውጤታማ የሆነ የዲፕሎማሲን መርህ የተከተለ አካሄድ ስኬታማነት ሁሉም በያለበት የበኩሉ ሊወጣ እንደምገባም ምሁራኑ ተናግረዋል።
ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በወላይታ ሶዶ ከተማ ከነዳጅ እጥረት ጋር በተያያዘ በህዝብ የትራንስፖርት አገልግሎት ላይ የነበረውን ክፍተት ለማረም...
Apr 30, 2026
ጅማ፤ ሚያዝያ 21/2018(ኢዜአ)፦ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የምርምር ሥራዎቻቸውን ከቀጣናዊ ተጨባጭ ሁኔታዎች ጋር በማስተሳሰር ዘላቂ ሰላምና የጋራ እድገት ለ...
Apr 30, 2026
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦የትራንስፖርት አገልግሎትን ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ተግባራዊ የተደረጉ ስልቶች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን የትራን...
Apr 29, 2026
ሀዋሳ ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡-ሀዋሳ ከተማን የቱሪዝምና የኮንፈረንስ ማዕከል በማድረግ ከተማዋ አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ እንድትሆን ርብርብ እየተደረ...
Apr 20, 2026