የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በክልሉ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜ ገንብቶ በማጠናቀቅ የግብርና ምርትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው

May 12, 2025

IDOPRESS

ወልቂጤ፤ ግንቦት 3/2017(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ ገንብቶ በማጠናቀቅ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ።

በክልሉ የም ዞን ከ600 በላይ አባወራዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የኮሾ አነስተኛ መስኖ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል።


በዚህን ጊዜ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ መሐመድ ኑሪዬ(ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በክልሉ በራስ አቅም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የህዝቡን ኑሮ ለማሻሻል ትኩረት ተሰጥቷል።

በዚህም የክልሉን የልማት አቅም ተጠቅሞ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በግንባታ ላይ ያሉ የመስኖ አውታሮች በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቁ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።


የተጀመረውን ሁለንተናዊ የብልጽግና ጉዞን ማሳካት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውንም አመልክተዋል።

የፕሮጀክት አመራርና አስተዳደርን በመፈተሽ በክልሉ የመስኖ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ ተገንብተው እንዲጠናቀቁ በማድረግ አርአያነት ያላቸው ተግባራት መከናወናቸውንም ተናግረዋል።

ለዚህም የኮሾ የመስኖ ፕሮጀክት በራስ አቅም ልማትን ማፋጠን እንደሚቻል ጥሩ ማሳያ መሆኑን ነው የገለጹት።


የኮሾ አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክት አርሶ አደሩን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ዓመቱን ሙሉ ማምረት የሚያስችለው ነው ያሉት ደግሞ የክልሉ ውሃ፣ መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዳዊት ኃይሉ ናቸው።

ግንባታቸው ተጓተው የነበሩ ፕሮጀክቶችን ችግር በመለየት ለውጤት እንዲበቁ እየተሰራ መሆኑንም አስታውቀዋል።


የክልሉ የመስኖ ተቋማት አስተዳደር ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ካሳዬ ተክሌ በክልሉ በ2017 በጀት ዓመት እየተገነቡ ካሉ 18 የመስኖ ፕሮጀክቶች ውስጥ ዘጠኙ መጠናቀቃቸውን ገልጸዋል።

ዘንድሮ በ87 ነጥብ 3 ሚሊዮን ብር ተገንብቶ ወደ ስራ የገባው የኮሾ አነስተኛ መስኖ ፕሮጀክት 150 ሄክታር መሬት የማልማት አቅም ያለው ሲሆን ከ600 በላይ አባወራዎችንም ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል።


የየም ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሺመልስ እጅጉ የመስኖ ልማት ለግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ እድገት የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመው፣ መስኖውን በአግባቡ በመያዝና በመጠቀም የህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚነት ለማጠናከር ይሰራል ነው ያሉት።


በዞኑ የሳጃ ደሪ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር እድሌ መርሻ እና አጥናፉ ወልደኢየሱስ በበኩላቸው ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግና ገበያን ለማረጋጋት የመስኖ ልማት ጉልህ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።

የመስኖ ፕሮጀክቱን በመጠቀም ማሽላ፣ በቆሎ እንዲሁም አትክልትና ፍራፍሬ ማልማት መጀመራቸውን ገልጸው፣ ፕሮጀክቱ ከዝናብ ጥገኝነት እንዳላቀቃቸው ተናግረዋል።


ከመስኖ ልማቱ ከቤት ፍጆታ ባለፈ ለገበያ የሚቀርብ ምርት በማምረት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ ተግተው እየሰሩ መሆናቸውንም ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.