የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሩዝ ምርት የማላመድና የማስፋት ሥራ እየተከናወነ ነው

May 21, 2025

IDOPRESS

ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 11/2017(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ለሩዝ ምርትና ምርታማነት ተስማሚ የሆኑ አካባቢዎችን በመለየት የማላመድና የማስፋፋት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ።

በወላይታ ዞን ዳሞት ሶሬ ወረዳ "ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ ዞናዊ የሩዝ ልማት የዘር መዝራት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ተካሂዷል።


በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ አድማሱ አወቀ ግብርናን በማዘመንና ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

በዚህም በክልሉ ያሉትን አቅሞች ለመጠቀም በተደረጉ ጥረቶች አበረታች ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑን ጠቁመው በአሁኑ ወቅት ደግሞ በክልሉ የሩዝ ልማትን የማላመድ ስራ ትኩረት ማግኘቱን ተናግረዋል።

ይህም የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማርጋገጥና የገቢ አቅሙን ለማሳደግ የሚያግዝ በመሆኑ በክልሉ ለሩዝ ልማት ተስማሚ በሆኑ አካባቢዎች ተግባራዊ የማድረግ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል።

የሩዝ ልማትን በክልሉ ለማላመድና ለማስፋት ታስቦ ዛሬ በወላይታ ዞን የተጀመረው የሩዝ ልማት በቀጣይም በሌሎች የክልሉ አካባቢዎች እንደሚጠናከር ገልጸዋል።


በዞኑ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሻሻል የሚደረገው ጥረት ጥሩ ውጤት እየታየበት መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የወላይታ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ እና የግብርና መምሪያ ኃላፊ ዳንኤል ዳሌ(ደ/ር) ናቸው።

በአካባቢው የሩዝ ልማት እንዳልተጀመረ አስታውሰው፣ ለማስለመድ በዞኑ ለምርቱ ተስማሚ የአየር ንብረት ያላቸው ሁለት ወረዳዎች ተመርጠው ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል።


በወላይታ ዞን የዳሞት ሶሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሙሉቀን መሸሻ በበኩላቸው ወረዳው ያሉትን አቅሞች በማሰባሰብ ልማቱን በማጠናከሩ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል።

በተለይ ችግሮችን በራስ አቅም መቋቋም አንዲቻል ለአደጋ ጊዜ መጠባበቂያ የሚሆን በ38 ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ ሰብሎች በመልማት ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።

በዛሬው ዕለትም በወረዳው ለሩዝ ምርት አመቺ በሆነ አካባቢ በሰባት ሄክታር ማሳ ላይ ልማቱ መጀመሩን ተናግረዋል።


አርሶ አደር መንቱ በቀለ መንግስት ያመቻቸውን ሁኔታ ተጠቅመው ውጤት ለማስመዝገብ እየተጉ መሆናቸውን ተናግረዋል።


አርሶ አደር ታምራት ገለቱም ባላቸው መሬት ላይ ሩዝ አልምተው ተጠቃሚ ለመሆን ሥራ መጀመራቸውን ገልጸዋል።

የሩዝ ምርጥ ዘርን በማባዛት በክልሉ የአየር ንብረቱ ተስመሚ በሆኑባቸው ሁሉም አካባቢዎች ለማድረስ ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኝም ተገልጿል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.