
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 18/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ብሔራዊ የዲጂታል ፍኖተ ካርታና የዲጂታል ጤና ስራ ክፍሎችን በማደራጀት ፈጠራን እንደ ስትራቴጂክ ችግር መፍቻ መቀበሏ ውጤት ለማስመዝገብ ዓይነተኛ ሚና መጫወቱን የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሂ ገለጹ።
ዓለም አቀፍ የጤና ኢኖቬሽንና ጥራት ጉባኤ "ኢኖቬሽን ለሁለንተናዊ የጤና ሽፋን" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል።

የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሂ፤ ኢትዮጵያ የኢኖቬሽን ጤና እንክብካቤ፣ የህሙማን ደህንነት፣ የጤና አገልግሎት ፍትሃዊነትና የጤና አመራርን ለማሳደግ መሰረት አድርጋ እየሰራች መሆኑን ተናግረዋል።
በጤናው ዘርፍ ባለፉት ዓመታት በርካታ ለውጦች መመዝገባቸውን አስታውሰው፤ በህክምና ተቋማት የሚወልዱ እናቶች መጠን ከ80 በመቶ በላይ፣ የክትባት ሽፋን ከ90 በመቶ በላይ መድረሱንና ሌሎች የተመዘገቡ ውጤቶችን ለማሳያነት ዘርዝረዋል።
ኢትዮጵያ ብሔራዊ የዲጂታል ፍኖተ ካርታና የዲጂታል ጤና ስራ ክፍሎችን በማደራጀት ፈጠራን እንደ ስትራቴጂክ ችግር መፍቻ መቀበሏ ለተመዘገቡ ውጤቶች ዓይነተኛ ሚና ተጫውቷል ነው ያሉት።
በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በሚደገፉ መመርመሪያዎች፤ ቴሌሜዲስንና ሰው አልባ መሳሪያዎች በጤናው ዘርፍ ማህበረሰብን ለመድረስ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።
በቀጣይም ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች፣ ወረርሽኝ፣ የጨቅላ ህጻናት ሞትንና ሌሎችን ለመቀነስ ፈጠራ የታከለበት አሰራርን በመዘርጋት ይበልጥ መስራት ይኖርብናል ብለዋል።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር)፤ ፈጠራ የቅንጦት ጉዳይ ሳይሆን በጤናው ዘርፍ በጥራት፣ ፍትሃዊነትና የታካሚዎች ደህንነት ላይ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን ለመሙላት ያግዛል ብለዋል።
ጤና ሚኒስቴር ያዘጋጀውን ስትራቴጂ መሰረት በማድረግ ዘርፉን የሚያሸጋግሩ የፈጠራ ስራዎችን በትብብር እያከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
በኢትዮጵያ የዓለም ጤና ድርጅት ተወካይ ዶክተር ኦውን ካሉዋ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ ሀገር በቀል የፈጠራ ውጤቶችን ተግባራዊ ማድረጓ ዘርፉን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር መሰረት ይሆናል ብለዋል።
የዓለም ጤና ስጋቶችን ተጽዕኖ የሚቋቋም የጤና ስርዓት ለመዘርጋት ፈጠራን ማዕከል ያደረጉ፣ ጥራትና ተደራሽነትን የሚያረጋግጡ አሰራሮችን መዘርጋት ወሳኝ መሆኑንም እንዲሁ።

የዓለም ጤና ድርጅት ባለፉት ዓመታት የኢትዮጵያን ብሔራዊ የጤና የፈጠራ ምህዳር ለማስፋት መደገፉን ጨምሮ በእናቶች ጤና አጠባበቅ ወባን በመቆጣጠር በዲጂታል ጤና አገልግሎት በቅርበት ሲሰራ መቆየቱን አስታውሰዋል።
ኢትዮጵያ ከነባራዊ ሁኔታዎች ጋር የተጣጣሙ ሀገር በቀል መፍትሔዎችን በፈጠራ በመደገፍ እያከናወነች ያለው ተግባር የጤናውን ዘርፍ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሻገር ቁልፍ ሚና እንዳለውም አመልክተዋል።
የዓለም ጤና ድርጅት በጤና ዘርፍ ፈጠራንና ሌሎች የጤና መርሃ ግብሮች የሚተገበሩ አሰራሮችን በመደገፍ ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር መስራቱን እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
ዓለም አቀፍ የጤና ኢኖቬሽንና ጥራት ጉባኤ ዛሬን ጨምሮ ለሶስት ቀናት የሚካሄድ ሲሆን፤ በጤናው ዘርፍ የተሰሩ የፈጠራ ውጤቶችን የሚያሳይ አውደ ርዕይ ቀርቧል።
ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በወላይታ ሶዶ ከተማ ከነዳጅ እጥረት ጋር በተያያዘ በህዝብ የትራንስፖርት አገልግሎት ላይ የነበረውን ክፍተት ለማረም...
Apr 30, 2026
ጅማ፤ ሚያዝያ 21/2018(ኢዜአ)፦ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የምርምር ሥራዎቻቸውን ከቀጣናዊ ተጨባጭ ሁኔታዎች ጋር በማስተሳሰር ዘላቂ ሰላምና የጋራ እድገት ለ...
Apr 30, 2026
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦የትራንስፖርት አገልግሎትን ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ተግባራዊ የተደረጉ ስልቶች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን የትራን...
Apr 29, 2026
ሀዋሳ ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡-ሀዋሳ ከተማን የቱሪዝምና የኮንፈረንስ ማዕከል በማድረግ ከተማዋ አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ እንድትሆን ርብርብ እየተደረ...
Apr 20, 2026