የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ኢንሼቲቮች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል

Oct 13, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

አዳማ፤ ጥቅምት 1/2018(ኢዜአ)፦ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ኢንሼቲቮች የተቀናጀ ርብርብ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ላሌ አመለከቱ።

የገጠር ልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር በ5ኛው ምዕራፍ አፈፃፀም ግምገማና በቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ ላይ ያተኮረ የምክር ቤቱ የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አመራሮችና አባላት የተሳተፉበት መድረክ በአዳማ ተካሄዷል ።


በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ላሌ እንደገለፁት በራስ አቅም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ ነው።

በልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር የታቀፉ የህብረተሰብ ክፍሎችም ህይወታቸውን ለማሻሻልና በምግብ ራስን የመቻልና ሠርቶ የማግኘት ባህል እንዲጎለብት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰዋል።

በተጨማሪም መርሃ ግብሩ በተለያየ ምክንያት የተራቆቱ መሬቶች እንዲያገግሙ እንዲሁም የመሬት ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ከማድረግ ባለፈ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ረገድ ትልቅ እገዛ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

በዚህም በተፈጥሮ ሀብት ልማት ጥበቃና እንክብካቤ የተሻለ አፈፃፀም መመዝገቡን የገለፁት አቶ ሰለሞን በመርሃ ግብሩ የታቀፉ ዜጎችም ጥሪት በማፍራት በምግብ ራሳቸውን ችለው በዘላቂነት ህይወታቸው እንዲለወጥ ማገዙንም አመላክተዋል።

በዚህም የተረጂነት አስተሳሰብ እንዲቀየር በማድረግ ረገድ መሰረታዊ ለውጥ እያመጣ ያለ መርሃ ግብር መሆኑን ጠቅሰው የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ኢንሼቲቮች የተቀናጀ ርብርብ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አመልክተዋል።

እየተተገበሩ ያሉ መልካም ጅምሮች በውጤታማነት እንዲቀጥሉ ምክር ቤቱ ለግብርና ዘርፍ እያደረገ ያለውን ድጋፍ፣ ክትትልና ቁጥጥር አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

የግብርና ሚኒስቴር አማካሪ ሚኒስትር ዴኤታ ኢፋ ሙለታ (ዶ/ር) በበኩላቸው የገጠር ልማታዊ የሴፍቲኔት መርሃ ግብር በአካባቢ ጥበቃ፣ በውሃ ማቆርና በአፈር ለምነት ላይ ትኩረት በማድረግ በ10 ክልሎችና በአንድ ከተማ አስተዳደር ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።


በተለይ በመንግሥት የተቀረፁ የግብርና ልማት ኢንሼቲቮች ግባቸውን እንዲመቱ መርሀ ግብሩ የራሱን በጎ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰዋል።

የመርሃ ግብሩ ተሳታፊዎችም የእንስሳት እርባታና ማድለብ እንዲሁም በንግድ በመሳተፍ ሠርተው ራሳቸውን ለመቻል እየተንቀሳቀሱ መሆኑን አመልክተው መርሀ ግብሩ የተረጂነት አስተሳሰብን በማስቀረት ጠንካራ የስራ ባህል እንዲጎለብት እያገዘ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.