
ዲላ ፤ ሐምሌ 16/2017(ኢዜአ)፦የዲላ- ቡሌ- ሐሮ- ዋጮ የ68 ነጥብ 7 ኪሎ ሜትር የአስፋልት መንገድ ግንባታን ለማጠናቀቅ የሚደረገው ጥረት መጠናከር እንዳለበት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ።
የጌዴኦ ዞንን የወከሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የዲላ-ቡሌ-ሐሮ-ዋጮ የአስፋልት መንገድ ግንባታ የስራ እንቅስቃሴን ምልከታ አድርገዋል።
በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ልማት ድርጅቶች ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ስብሳቢ ኢንጂነር ስለሺ ኮሬ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት የአስፋልት መንገድ ግንባታው መጠናቀቅ ለአካባቢው ሁለንተናዊ ለውጥ ድርሻው የጎላ ነው ።
በምልከታቸው የግንባታው ሂደት በጥራት እየተከናወነ ቢሆንም በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ ይበልጥ መሰራት አለበት ብለዋል።
ፕሮጀክቱን በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ በሚደረገው ጥረትም የአካባቢው ህብረተሰብ የሚያደርገውን ድጋፍ ማጠናከር እንዳለበትም ተናግረዋል።

የመንገዱን ግንባታ በአራት ዓመት ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ ውል ታስሮ በ2015 ዓ/ም ወደ ስራ መገባቱን ያነሱት ደግሞ የግንባታ ፕሮጀክቱ አማካሪ ድርጅት ኃላፊ ኢንጂነር ሉላዊ አያሌው ናቸው።
ይሁንና ባለፉት ሁለት ዓመታት የግንባታ ፕሮጀክቱ ከሚሸፍነው 68 ነጥብ 7 ኪሎ ሜትር ውስጥ 6 ኪሎ ሜትር ብቻ መሰራቱን አንስተው ለዚህም የወሰን ማስከበር ስራው ችግር ሆኖ መቆየቱን ገልፀዋል።
በአሁኑ ወቅት ግን የአካባቢው አስተዳደርና የክልሉ መንግስት በቅንጅት ችግሩን ፈተው የግንባታ ሂደቱ እየተፋጠነ እንደሚገኝም አንስተዋል።

በተለይ የአፈር ስራ፣ የግብዓት ዝግጅትና የፍሳሽ መውረጃ ቦዮች ስራ እየተፋጠነ መሆኑን አንስተው የአስፋልት ማልበሱን ስራ በአጭር ጊዜ በመጀመር ፕሮጀክቱን በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ እየተሰራ ነው ብለዋል።
የጌዴኦ ዞን ትራንስፖርትና መንገድ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ስለሺ ሽፈራው በበኩላቸው መንገዱ የዲላንና የቡሌ ወረዳዎች እንዲሁም በምስራቅ ጉጂ ዞን በኩል ዳማና ኡራጋ ወረዳዎችን የሚያስተሳስር መሆኑን አስረድተዋል።
ይህም የግብርና ምርቶችን ወደ ገበያ ለማውጣት በማገዙ ለአካባቢው ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት ወሳኝ ሚና እንደሚጫወት አመልክተዋል።
ለዚህም የመንገዱን ግንባታ ለማፋጠን የዞኑ አስተዳደር የግንባታ ግብዓት ማምረቻ ቦታ ከይገባኛል ነጻ በማድረግ ለአስፋልት ስራው መፋጠን የድርሻውን እየተወጣ እንደሚገኝም ነው ያነሱት።

በጌዴኦ ዞን የቡሌ ከተማ ነዋሪ አቶ አብርሃም ሃይሉ በበኩላቸው ቀደም ሲል በአካባቢያቸው የመንገድ መሰረተ ልማት እጥረት በመኖሩ የአካባቢው ልማት እንዲጓተት ምክንያት ሆኖ መቆየቱን ጠቁመዋል።
አሁን ላይ የአስፓልት መንገዱ ግንባታ በመጀመሩ ይዞታቸውን በወቅቱ በማንሳት ለስኬቱ የድርሻቸውን መወጣታቸውን ገልፀዋል።
አዲስ አበባ፤ሰኔ 2 /2018 (ኢዜአ)፦የዕቃ ማከማቻ ደረሰኝ ሥርዓት ደንብ የግብርና ኢኮኖሚ ሽግግርን በማሳለጥና የገጠር ልማትን በማጎልበት አርሶ አደሮችን ተጠ...
Jun 10, 2026
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በመዲናዋ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥን በማላቅ የተገልጋዮችን እርካታ የሚያሳድጉ ሰው ተኮር ተግባራት ተጠናክረው እንደ...
Jun 9, 2026
ሀዋሳ ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦በይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ማቀነባበሪያ ፓርክ ከአምራች ኢንዲስትሪዎች ጋር በተፈጠረላቸው የገበያ ትስስር ...
Jun 6, 2026
ነገሌ ቦረና፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት መጀመር የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የበለጠ የሚያ...
May 28, 2026