አዲስ አበባ፤ የካቲት 4/2017(ኢዜአ)፡-ኢትዮ-ቴሌኮም ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን የሚያደርጉ ቴክኖሎጂዎችን ተግባራዊ የማድረግ ስራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታወቀ።
ኢትዮ-ቴሌኮም የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ባትሪ በፍጥነት መሙላት የሚያስችሉ ሶስት የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችን ዛሬ ይፋ አድርጓል።
ቴክኖሎጂዎቹ ተግባራዊ የሚደረጉበት የራሱ የሆነ የሀይል ማስተላለፊያ ጣቢያ የተዘጋጀለት ሲሆን፤ ይህም በአዲስ አበባ ከመገናኛ ወደ ቦሌ በሚወስደው መንገድ ኢምፔሪያል አካባቢ የሚገኝ ነው።
የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ በወቅቱ እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ሥራ ላይ የዋሉት ቴክኖሎጂዎች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ናቸው።
ይህም የተጀመረውን ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን የማድረግ ጉዞን የሚያረጋግጥና በተግባር የሚያሳይ መሆኑን ተናግረዋል።
ከቴክኖሎጂዎቹ መካከል "አልትራ ፋስት" የተሰኘው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ባትሪ መሙያ አንድ ኪሎ ሜትር መጓዝ የሚያስችል ሀይልን በአንድ ሰከንድ እንደሚሞላ ተናግረዋል።
በተጨማሪም "ሱፐር ፋስት" የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ባትሪ መሙያ ቴክኖሎጂ ከ10 እስከ 30 ደቂቃ ድረስ ሙሉ ሀይል ለመሙላት እንደሚያስችል ገልጸዋል።
ሌላኛው የሀይል ማስተላለፊያ ቴክኖሎጂ ደግሞ ድንገተኛ የሀይል መቋረጥ ሲያጋጥም በሀይል ማስተላለፊያ ጣቢያ ውስጥ ባሉ ፖሎች ላይ በተገጠሙ ቴክኖሎጂዎች አማካኝነት በቀላሉ ሀይል መስጠት የሚያስችል ስለመሆኑም ዋና ስራ አስፈፃሚዋ አክለዋል።
ዘመናዊ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ባትሪ መሙያ ጣቢያዎቹ በአንድ ጊዜ እስከ 32 የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን የማስተናገድ አቅም ያላቸው ሲሆን፤ ክፍያው በቴሌ ብር የሚፈጸም ይሆናል ብለዋል።
በአሁኑ ወቅት በከተማዋ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቁጥር እየጨመረ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ የባትሪ መሙያ ቴክኖሎጂዎች ውስንነትና ፍጥነት ችግር እንደሚስተዋል ጠቁመዋል።
እነዚህ ቴክኖሎጂዎች ዘመናዊ አኗኗርን በማለማመድና ጊዜን በመቆጠብ ረገድ ፋይዳቸው የጎላ መሆኑን ዋና ስራ አስፈጻሚዋ አክለዋል።
በሌላ በኩል ኢትዮ-ቴሌኮም የተቋቋመበትን 130ኛ ዓመት ክብረ-በዓሉን ምክንያት በማድረግ ያዘጋጀውን እጣ ላሸነፉ ግለሰቦች ሁለት ዘመናዊ ተሽከርካሪዎችን ሸልሟል።
አዲስ አበባ ፤የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር ትራንስፖርት ተገልጋዮች ፋይዳ መታወቂያን ተጠቅመው በዲጂታል አማራጭ ትኬት የሚቆርጡበት አሰራር ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ ጥር 03/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለስልጣን የለማ የትራንስፖርት ኦፕሬተሮችንና የጭነት ባለቤቶችን የሚገናኝ መተግበሪያ አስጀምሯል። ...
Feb 12, 2025