የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ህይወት እና ጉዞ

<p>ለሕዳሴው ግድብ የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሚዛን አማን ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ</p>

Feb 14, 2025

IDOPRESS

ሚዛን አማን፤ የካቲት 6/2017(ኢዜአ)፡- ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የቤንች ሸኮ ዞን የሚዛን አማን ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ።

የቤንች ሸኮ ዞን አስተዳደር በበኩሉ ለሕዳሴው ግድብ ግንባታ የመጨረሻ ምዕራፍ ሥራ የሚውል 8 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ለማሰባሰብ እየሠራ መሆኑን አስታውቋል።


አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ የሚዛን አማን ከተማ ነዋሪዎች መካከል አቶ ሰሎሞን ማቴዎስ፣ የሕዳሴው ግድብ ሁሉንም በአንድ ያስተሳሰረ የአብሮነት ፕሮጀክታችን ነው ሲሉ ተናግረዋል።

ከዚህ ቀደም ለሁለት ጊዜ ቦንድ መግዛታቸውን አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅትም ከደመወዛቸው ቦንድ ለመግዛት መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።

የሕዳሴው ግድብ የኢትዮጵያውያን የእንችላለን ወኔ ነጸብራቅ ነው ያሉት ደግሞ አቶ ተሰማ ሻሪ የተባሉ የከተማዋ ነዋሪ ናቸው።

በጫና ውስጥ ግድቡን መገንባት የተቻለው ኢትዮጵያውያን አብሮነታቸውን በማጠናከራቸው እንደሆነ ገልጸው፣ በሌሎች የልማት ሥራዎችም ሕብረትን ማጠናከር ይግባል ብለዋል።


ወይዘሮ ፋንታነሽ ካሳ የተባሉ ሌላኛዋ ነዋሪ በበኩላቸው፣ የሕዳሴው ግድብ የግንባታ ሥራ ከተጀመረ አንስቶ ቦንድ በመግዛት የድርሻቸውን ሲወጡ መቆየታቸውን ገልጸዋል።

በቀጣይም የግድቡ ግንባታ ተጠናቆ ለአገልግሎት እስኪበቃ ድረስ ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል።

የሕዳሴው ግድብ የእኛ ዘመን ትውልድ አሻራ ያረፈበትና ዘመን የሚሻገር ፕሮጀክት በመሆኑ በቦንድ ግዥና በተለያዩ መንገዶች የምናደርገው ድጋፍ መቀጠል አለበት ብለዋል።


ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የሁሉም አሻራ ያረፈበት የጋራ ሀብታችን ነው ያሉት ደግሞ የዞኑ አስተዳደር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ እሸቱ ሻንበል ናቸው።

የግድቡ ግንባታ የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ በመድረሱ ትልቅ ኩራት እንደሚሰማቸው ገልጸው፣ ቀሪ ሥራዎችን ለማጠናቀቅ በዞኑ የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።

በሁለት ወራት ጊዜ ውስጥ ከማህበረሰቡ 8 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር ገቢ ለማሰባሰብ ታቅዶ በሁሉም መዋቅሮች ገቢ የማሰባሰብ ሥራ መጀመሩን ተናግረዋል።

ከዚህ ቀደም በተለያዩ ጊዜያት ከዞኑ 38 ሚሊዮን ብር ድጋፍ መደረጉን አስታውሰው፣ በቀሪ ጊዜያትም ድጋፉን አጠናክረው ለማስቀጠል ይሰራል ብለዋል።

ህብረተሰቡ ድጋፉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ከማስተባበር ባሻገር በራሳቸው የ5 ሺህ ብር ቦንድ ግዥ ለመፈጸም ቃል መግባታቸውን የገለጹት ኃላፊው፣ ዕቅዱን ለማሳካት የተጠናከረ ሥራ ይሰራል ነው ያሉት።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.