አዲስ አበባ ፤ የካቲት 24/2017 (ኢዜአ)፡- የጃፓን ዓለም አቀፍ የትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) በኢትዮጵያ የግብርና ምርታማነት እና የግብይት ስርዓትን ለማጎልበት እያደረገ ያለውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታወቀ።
የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ከጃፓን ዓለም አቀፍ የትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) ምክትል ፕሬዝዳንት ያማጉቺ ሂሮዩኪ ጋር በጽህፈት ቤታቸው ተወያይተዋል።
ውይይቱ ሁለቱ ወገኖች በግብርናው ዘርፍ በጋራ መስራት በሚችሉባቸው ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነው።
ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ጃይካ በኢትዮጵያ በሆርቲካልቸር እና በሌሎች የግብርና መስኮች ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በምግብ ራስን ለመቻል በጀመረችው ጉዞ ሩዝ በስፋት ማምረት መጀመሯንና በዚህም 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በዘር መሸፈኑን አመልክተዋል።
ለሩዝ ልማት ተስማሚ ስነ-ምህዳር መኖሩን የገለጹት ሚኒስትሩ ጃይካ በሩዝ ልማት ያለውን ልምድ በመጠቀም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግና ቴክኖሎጂን ከማስፋፋት አኳያ የበለጠ ድጋፍ እንዲያደርግ ጠይቀዋል።
ሚኒስትሩ 70 በመቶ የሚጠጋው የወጪ ንግድ የግብርና ምርቶች መሆናቸውን ጠቅሰው የግብርና ግብይትን ለማጠናከር ድጋፍ እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።
የጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) ምክትል ፕሬዝዳንት ያማጉቺ ሂሮዩኪ በበኩላቸው ጃይካ በኢትዮሼፕ በሆርቲካልቸርና በሌሎች ዘርፎች ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
አርሶ አደሮችን ለማበረታታት፣ የሩዝ ልማት ቴክኖሎጂዎችን ለማስፋት እና የባለድርሻ አካላትን አቅም ለማሳደግ እየሰራ ነው ብለዋል።
በቀጣይም የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግና የግብርና ግብይትን ለማጠናከር ድጋፍ እንደሚደረግ አመልክተዋል።
ጃይካ በግብርናው ዘርፍ በተለይም በሆርቲካልቸር እና በሩዝ ልማት፣ በተፈጥሮ ሀብት፣ በአየር ንብረት፣ እንዲሁም በስርዓተ ምግብ እና በግብርና ኢንሹራንስ ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር እየሰራ እንደሚገኝ ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
አዲስ አበባ ፤የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር ትራንስፖርት ተገልጋዮች ፋይዳ መታወቂያን ተጠቅመው በዲጂታል አማራጭ ትኬት የሚቆርጡበት አሰራር ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ ጥር 03/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለስልጣን የለማ የትራንስፖርት ኦፕሬተሮችንና የጭነት ባለቤቶችን የሚገናኝ መተግበሪያ አስጀምሯል። ...
Feb 12, 2025